(‘ሐሳቦች መዘዝ አላቸው’ በሚል ርእስ በኤማሁስ መጽሔት ቅጽ 1 ፣ ቁጥር 1 በወጣው ጽሑፍ ላይ የተጻፈ አስተያየት)
በመሐሪ ዘመልአክ (PhD)
ከዛሬ አሥራ አምስት ዓመታት በፊት የእጓለ ገብረ ዮሐንስ ‘የከፍተኛ ትምህርት ዘይቤ’ ለመጀመሪያ ጊዜ ካነበብኹ በኋላ ጸሐፊውን ከዚያ በፊት አለማወቄ ገርሞኝ እንደነበር አስታውሳለኹ ። ማን ናቸው ? እንዴት እስከዛሬ ድረስ ስለእርሳቸው ሳልሰማ ቀረኹ ? ለምን ? ይኼ በ1956 ዓ.ም. የታተመ የሬድዮ ንግግር ከኾነ መጽሐፍ ለመጻፍ ብለው ተነሥተው ቢጽፉ ኖሮ ምን ሊጽፉ ነበረ ? ወዘተ. የሚሉ ጥያቄዎች ጭንቅላቴ ውስጥ ተመላልሰዋል ።[1] በኋላ ፈላስፋው ኦርቶዶክሳዊ አማኝ ፣ የኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ተማሪና መምህር እንደነበሩ ስሰማ በመጽሐፉ ውስጥ ያየሁት የሐሳብ ጥልቀት በዘመኑ በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ልሒቃን ዘንድ የነበረው ተዋሥኦ ሊደርስ ይንጠራራበት የነበረውን ልክ የጠቆመኝ መሰለኝ ።
ከዚያ በኋላ ያ የተዋሥኦ ልሕቀት የት ገባ ? እንዴት ድርቅና የተጫነው ተዋሥኦ ዋጠው ? እንዴት ኦርቶዶክሳዊነትን ከአመክንዮ የተፋታ እና አመክንዮን የሚፈራ ጭፍን እምነት የሚያስመስሉ የፎክሎር ሰባኪዎች ተፈለፈሉብን ? የኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ካህን ለመኾን የሚጠየቀው መስፈርት ስለምን ድፍረት የለበሰ አላዋቂነት መሰለ ? በሚዲያ ላይ ሲናገሩ በአላዋቂነታቸው አንገታችንን የማያስደፉን ካህናት ስለምን ቁጥራቸው አልበረክት አለን ? ኦርቶዶክሳዊነት ችግርን እና ጭንቀትን ለማረሳሳት የተጠመቀ ዕፀ-ዝንጋዔ (‘opium of the masses’) እስኪመስል ድረስ በኦርቶዶክሳዊነት ስም የገነነው ተዋሥኦ ለምን አላዋቂነት ተጫነው ? ቤተ ክርስቲያን ሲባል ከስሜታዊ ሙጥኝታ (sentimental attachment) ባለፈ ለሰው ልጅ ህልውናዊ ጥያቄ የተሰጠ ከሞት ፍርኃት በላይ ኾኖ የመኖር የሕይወት አማራጭ እንደኾነ የሚያሳይ ተዋሥኦ ራቀን ? የእጓለ ገብረ ዮሐንስን እምነትና አመክንዮ የተሰናሰሉበትን ኦርቶዶክሳዊ ተዋሥኦ አስቀጥለን ቢኾን ኖሮ እነዚኽ ከላይ የጠቃቀስኋቸው ሕመሞቻችን ይደርሱብን ነበረ ? እነዚኽን ጥያቄዎች የማነሣው በዚኽ ጽሑፍ መልስ ለመስጠት ሳይሆን ባለፉት 75 ዓመታት ኦርቶዶክሳዊው ተዋሥኦ የደረሰበትን ድቀት እንድናስተውለው ጥቂት ታዋቂ ቁስሎቻችንን ነካክቼ ሕመሙን ለማስታወስ እና የኤማሁስ መጽሔት ላይ የሚተጉት ለጋ እጆች ሊገምዱት የሚታትሩትን የተዋሥኦ ገመድ ከእጓለ ገብረ ዮሐንስ ተዋሥኦ ጋር ሰባ ዓመታት ወደ ኋላ ኼጄ የታሪክ ድራቸውን አንድ ላይ ልቋጥር ፈልጌ ነው ።
ይኽ ድር የተገመደው አሚን (faith) እና አመክንዮ (reason) ከሚባሉ ኹለት ክሮች ነው ። ከአመክንዮ የተፋታ እምነት ወደ ጥንቆላነት (superstition) ይወርዳል ። ከእምነት የተፋታ አመክንዮ ደግሞ መንፈሳዊው (spiritual)ን በስሜት (emotion)፣ ሰብአዊውን (human) በቁሳዊው (material) አጣፍቶ ሰውን ለቀቢጸ ተስፋ (nihilism) መንጋጋ ያስረክባል ። እስካሁን ከሰማኋቸው ፖድካስቶቻቸው በመነሣት የኤማሁሳውያን ሕልም በእምነት የበለፀገ አመክንዮ እና በአመክንዮ የጠራ እምነት ላይ የተሠራ የኦርቶዶክሳዊነት ተዋሥኦ መገንባት ይመስለኛል ። ሙግቶቻቸው ክርስቶስን ማዕከል ያደረጉ (Christocentric) ፣ ጥንታውያኑን አበውን ያገናዘቡ ፣ ከሐዋርያዊ ክርስትና ፍንክች ላለማለት የቆረጡ ናቸው ።
የኤርምያስ ክንዴ ‘ሐሳቦች መዘዝ አላቸው’ የሚል መጣጥፍ ይኽን ከምናይባቸው ጽሑፎች አንዱ ነው ። ኤርምያስ የነገረ ጾታን (የጾተኝነትን) ተዋሥኦ በማኅበራዊ ሚዲያ ከሚታየው አላዋቂነት ፣ ተንጨርጫሪነትና ተንጰርጳሪነት ከሚመሩት ጫጫታ አውጥቶ ነገሩን ከሥሩ አጥርቶ ለማሳየት ይሞክራል ። ድኅረ ዘመናዊነት ፣ ጾተኝነት (gender ideology) እና ከሰው-ባሻገሬነት (transhumanism) የቆሙባቸው ፍልስፍናዊ መሠረቶች በውስጣቸው ያለውን ኢተጠየቃዊነትና ተፋልሶ በማሳየት ኦርቶዶክሳዊ ክርስትና ቀናይቱን ህልውናዊ አማራጭ እንደሚያቀርብ ይጠቁማል ። የኤርምያስ መጣጥፍ ኹለት መሠረታዊ የሙግት ነጥቦች ነገረ ሰብእ (anthropology) እና ነገረ ዕውቀት (epistemology) ኾነው ታይተውኛል ።
ከነገረ ዕውቀት አኳያ ሲፈተሹ ፥ በጥቅሉ የድኅረ ዘመናዊነት አስተሳሰቦች በተለይም ደግሞ የጾተኝነት ርእዮተ ዓለም (gender ideology) “የማውቀው የሚሰማኝን ነው ፤ ስለዚኽም እውነት ማለት እኔ የተሰማኝ ነገር ነው ።” የሚል መሠረት ላይ ይቆማሉ ። ኤርምያስ ሌሎች ይኽን አስተሳሰብ የሞገቱ ዕውቅ ክርስቲያን ጸሐፊዎችን ተተግኖ ይኽንን የድኅረ ዘመናዊነት ዓምድ ስሕተት ይጠቁማል ። ይኽ የድኅረ ዘመናዊነት መንገድ ማኅበረሰባዊ ሥልጣኔ ሳይኾን እውነትን በማኅበር ተሰብስቦ የመካድና ማለቂያ ወደሌለው ውዥንብር የመገሥገሥ እብደት ነው ። የአስተያየት አገዛዝን የማስፈን ፣ ወይም የአንጻራዊነትን አምባገነንነት የማንገሥ ጉዞ (Dictatorship of relativism) ነው ።[2] ኤርምያስ በዚህ መንገድ የሚደረግ ጉዞ የሰውን ልጅ በእውነት አልባነት በረኀ ውስጥ ወደመሞት እንደሚያደርሰው ያስጠነቅቃል ።
ኹለተኛው ነጥብ ነገረ ሰብእን የሚመለከት ነው ። ኤርምያስ የጾተኝነት ርእዮተ ዓለም ለሰው ልጅ የሚሰጠው ብያኔ የሰውን ልጅ ማንነትና ክብር የማይገልጥ ስሑት ብያኔ እንደኾነ ይጠቁማል ። ጾተኝነት የሰው ብያኔውን የቀዳው ከእነ ኒቼና ሳርት ፀረ እግዚአብሔር ህልውናዊነት (atheist existentialism) ነው ። በዚያ የሐሳብ ፈለግ ደግሞ ሰው ራሱን የመፍጠር ፍዳ የተጣለበት ትርጉም አልባ ነገር ነው ። እነርሱ እንደሚሉት መነሻው አጋጣሚ መድረሻው ደግሞ ምንምነት ስለኾነ በዚኽ ወይም በዚያ መንገድ መኖሩ የሚያመጣው ምንም ዓይነት የሞራል ዕሴት የለም ፤ እንዲያውም እግዚአብሔር እና ሞራል የሚባሉ ሐሳቦች ሰው ፍላጎቶቹን እየተከተለ ራሱን እንዳሻው አድርጎ እንዳይፈጥር ዕንቅፋት ይኾኑበታል ፤ ስለዚኽ እነዚኽን ጠላቶቹን አሽቀንጥሮ ጥሎ በኢሞራላዊነት ፍላጎቶቹን ብቻ እየተከተለ ያሻውን ማድረግ አለበት ፤ ያሻውን ደጋግሞ በማድረግም ያሻውን መኾን ይችላል ።
ይኽ ፀረ እግዚአብሔር ህልውናዊነት ከውጪ ሲያዩት ሰውን የሚያከብር ፥ ለሰው ልጅ ቅድሚያ የሚሰጥ ይመስላል ። ነገር ግን ፥ ውስጡ ሲታይ እጅግ አደገኛና የሰውን ልጅ ራሱ በትርጉም አልባነት ራሱን እንዲጠላ የሚያደርግና ምናልባትም የሰውን ልጅ ሕይወት ከመናቅና ከመጥላት የመጣ አስተሳሰብ ይመስላል ፤ ዣን ፖል ሳርት “Hell is other people”[3] (ሲዖል ማለት ሌሎች ሰዎች ናቸው) እንዲል ። ጾተኝነትን ‘አሜን’ ብሎ የሚቀበል ሰው ይኽን ‘የሰው ልጅ ሕይወት ትርጉም አልባ ነው’ የሚለውን ነገረ ሰብእ ቢያውቀውም ባያውቀውም ‘አሜን’ ብሎ ይቀበለዋል ፤ የጾተኝነት ርእዮተ ዓለም የቆመበት መሠረቱ ነውና ።
ኤርምያስ ይኽን የጾተኝነትን ርእዮተ ዓለም መሠረት ለማፍረስ ኦርቶዶክሳዊ ክርስትና ለሰው ልጅ የሚሰጠውን ብያኔ በማንጸሪያነት ያቀርባል ። የሰው ልጅ ለትርጉም አልባ ፍጻሜ ራሱን የመፍጠር ዕዳ የተሸከመ ነገር አይደለም ። በክርስቶስ ሙላት ክርስቶስን መስሎ ፥ ከእግዚአብሔር ጋር ፣ በእግዚአብሔር ውስጥ ፣ ለእግዚአብሔር ክብር በመኖር ፥ በእግዚአብሔር ጸጋ አምላክ እንዲኾን የተፈጠረ የእግዚአብሔር መልክ ነው ፤ “ከሰዎች መካከል አማልክት ይኾኑ ዘንድ ለሚያምኑብኽ ቅን ኅሊናን የፈጠርኽ”[4] እንዲል ። ይኽ ብያኔ ሴት ወይም ወንድ ፣ ግሪካዊ ወይም አሜሪካዊ ፣ ሀብታም ወይም ድኃ ፣ ወዘተርፈ መኾንን ለሰው ልጅ መበየኛነት አይወስድም ። ከሰውነት የማሳነስ ወይም የማተለቅ ሚናም አይሰጣቸውም ። ክርስቲያናዊው ብያኔ የሰው ልጅ በምንም ኹኔታ ውስጥ ይኹን ፥ የትም ይኑር ፥ ሰው መኾን አለመኾኑን ፥ እንደሰው እየኖረ መኾን አለመኾኑን የሚለካው በክርስቶስ ኑሮ ልክ ነው ። ሰው የመኾን ልኩና ግቡ የእግዚአብሔር ልጅነት ስለኾነ እንደሰው መኖራችን የሚለካው በእግዚአብሔር ልጅ በኢየሱስ ክርስቶስ ኑሮ መጠን ነው ። ከእርሱ ያነሰ ልክና ሚዛን ለሰው ልጅ አይመጥነውም ። የሰው ልጅነት ማለት የእግዚአብሔር ልጅ መኾን የሚችል ፍጡር ነው ። የተፈጠረበት ዓላማ ፣ የሚኖረው ኑሮ ትርጉሙ ፣ ልኩ ፣ መልኩ ኢየሱስ ክርስቶስ ነው ። ኦርቶዶክሳዊው የህልውና አማራጭ ይኽ ነው ።
የኤርምያስ ሙግት አሌክሳንደር ፑሽኪን እና የሞስኮ ጳጳስ የነበሩት ፊላሬት በግጥም ያደረጉትን ምልልስ ያስታውሰናል ። አንድ ቀን ፑሽኪን ጨለምተኝነት ጎበኘውና እንዲኽ ብሎ ገጠመ፦
Useless gift, accidental gift,
Life, why were you given me?
Why are you given by fate’s secret will
As punishment or as reward?
Who sent you down to me?
Death’s enigma or life’s mocking breath?
I do not know you — what use are you?
Or why do I suffer and die?
ግጥሙም የብዙዎችን በባዶነት ጩኸት የሚሰቃይ ሐዘንተኛ ልብ ነካው መሰል ብዙዎች ወደዱት ። በዚኽ ጊዜ ሊቀ ጳጳሱ ፊላሬት እንዲኽ ሲሉ በይፋ ለፑሽኪን መልስ ሰጡ፦
Not in vain and not by chance
Was life’s gift given to you.
Not without the will of Heaven
Did your soul begin to burn.
In yourself — look, and discover:
Both the source of pain and hope.
Believe: from Heaven’s highest realm,
God watches over every soul.
ፑሽኪን ይኽን ግጥም አንብቦ ሐሳቡን በይፋ ቀይሯል። ኤርምያስም ገብቷቸውም ይኹን ሳይገባቸው ጾተኝነትን ሙጥኝ ያሉትን አለቃቃሽ ነፍሶች ሐሳባቸውን ይቀይሩ ዘንድ ይጣራል ፤ የሰው ልኩ ክርስቶስ ነውና ።
፨ ፨ ፨
[1] “ብፁዓን ንጹሐነ ልብ” የሚለውን ሥራቸውንም አንዘነጋም።
[2] “The tyranny of relativism” Benedict XVI, Light of the World: The Pope, The Church and The Signs Of The Times. A Conversation with Peter Seewald (San Francisco: Ignatius Press, 2010), 50-54.
[3] Sartre, Jean-Paul, No Exit: A Play in One Act (United Kingdom: French), 1958.
[4] “ዘፈጠርከ ኅሊናተ ርቱዓተ ለእለ የአምኑ ብከ ከመ እምሰብእ ይኩኑ አማልክተ” የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን፣ “መጽሐፈ ኪዳን፣” in መጽሐፈ ቅዳሴ፤ መዝገበ፡ ቅዳሴ፡ ዘደብር፡ ዓባይ (አዲስ አበባ፤ ትንሣኤ የመጻሕፍት ማተሚያ ድርጅት፣ 1984).






ቃለ ሕይወት ያሰማልን እኔም “ሐሳቦች መዘዝ አላቸው” የሚለውን ካነበብኩ በኋላ የተሰማኝ ይህ ነበር እርሶ በመልካም ቃል ገልጠውታል። የኔን ዘመን ወጣት አለማንበብ ርእዮቶችን ጠለቅ ብሎ አለመፈተሽ ወደ ማይነሳበት ውድቀት እየመራው ነው።
It is nice especially for current generation and it is better to continue
በዶክተሩ ጽሑፉ ከተነሳው ሐሳብ በተጨማሪ በፈረንጅ አፍ የሚታወቁትን ቃላትና ሐረጋት ወደ ሀገርኛ ቋንቋ የተመለሱበት መንገድ ይማርካል።
እግዚአብሔር ይስጥልን
ጥሩ እየታና አስተያየት ነው።