“ከጥያቄው በላይ አደገኛ መልስ” ይሆንን?

ኤማሁስ ፕሬስ በተባለ አንድ የኤሌክትሮኒክ ሚዲያ ላይ “ከጥያቄዎቹ በላይ አደገኛ የሆኑት መልሶች” በሚል ርእስ የተጻፈ ጽሑፍ አንድ ወዳጄ አጋርቶኝ አነበብኩ። ለኦርቶዶክሳዊት ቤተ ክርስቲያን ከልባቸው የሚጨነቁና የሚቀኑ ወንድሞች በመጻፋቸው ደስ ብሎኛል። ይህ እንደ ተጠበቀ ሆኖ፣ በጽሑፉ ሐሳብና መንፈስ ላይ ግን አስተያየቴን እንድሰጥ ግድ ብሎኛል።
ዘነበ ወላ የተባለው ግለሰብ በተናገረው ነውረኛ ሐሳብ ላይ በጊዜው የጻፍኳትን ትንሽ ጽሑፍ “ተገቢ ያልሆነ” ብለዋታል። ከዚህም በላይ “ከጥያቄዎቹ በላይ አደገኛ የሆኑት መልሶች” ብለው ፈርጀዋታል። ወንድማዊ ብያኔ ስለሆነ ችግር የለውም። ግን ይህች አስተያየት የጻፍኩት እንደዚያ ከማሰኘት የሚያደርሰው ነገር ስላልታየኝ ነው።

እንደ ገባኝ ከሆነ፣ ዋናው ትችት፣ ጽሑፉ ገዳማዊ ሕይወት በኢኮኖሚ፣ በታሪክና መሰል ዘርፎች ያደረጋቸው አስተዋጽኦዎች መጠቀሳቸውና በዚህ አንጻር መልስ መሰጠቱ፣ ገዳማዊ ሕይወትንና ክርስትናን ወደ ምድራዊ እሳቤና መለኪያ ዝቅ የሚያደርግ (reductionist) ነው የሚል ነው። ግን እንደዚህ ብሎ ለመደምደም ይቻላልን?
ለስም አጠራሩ ክብርና ምስጋና ይግባውና ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሰዱቃውያን ቀርበው ስለ ትንሣኤ ሙታን ጉዳይ ጥያቄ በጠየቁት ጊዜ የመለሰላቸው “ስለ ትንሣኤ ሙታን ግን፣ እኔ የአብርሃም አምላክ፣ የይስሐቅም አምላክ የያዕቆብም አምላክ ነኝ የሚል ከእግዚአብሔር ዘንድ ወደ እናንተ የተባለውን አላነበባችሁምን? የሕያዋን አምላክ ነው እንጂ የሙታን አይደለም” ብሎ ነበር። ማቴ. 22፡31-32 ይህ ጌታችን የጠቀሰው ቃል የሚገኘው በኦሪት ዘጸአት 3፡6 ነው። ጌታችን ስለ ትንሣኤ ሙታን ጉዳይ ላነሡት ጥያቄ ሲመልስላቸው፣ ስለ ትንሣኤ ሙታን በግልጽ ከተናገሩት ከነቢያት መጻሕፍት በመጥቀስ ፋንታ ለምን ከዘጸአት ጠቀሰላቸው? ብንል ምክንያቱ ሰዱቃውያን ከአምስቱ የሙሴ መጻሕፍት በቀር የነቢያትን መጻሕፍት ስለማይቀበሉ ነበር። ስለዚህ ከሚቀበሉት መጽሐፍ ጠቅሶ ስህተታቸውን አስረዳቸው አንጂ ከማይቀበሉት መጻሕፍት ጠቅሶ ላስረዳችሁ አላለም።

ሆኖም ለሰዱቃውያን ከነቢያት መጻሕፍት አለመጥቀሱ ግን የእነርሱን ስህተት በማጽደቅ ወይም ወደ እነርሱ እሳቤ ዝቅ በማለት (reductionism) ያስወቅሰዋልን? ኧረ በጭራሽ! መድኃኒት የሚሰጠው እንደ ሕመሙ ሁኔታና በሽተኛው በሚያስፈልገው ልክ እንጂ በሐኪሙ እውቀት ልክ አይደለምና! አስፈላጊ በሆነበት ጊዜ ደግሞ “እኔ ሕግንና ነቢያትን ለመሻር የመጣሁ አይምሰላችሁ” እያለ አስተምሯል። ማቴ. 5፡17
ወንጌላዊው ቅዱስ ማቴዎስ ወንጌልን ሲጽፍ የጀመረው “የዳዊት ልጅ፣ የአብርሃም ልጅ፣ የኢየሱስ ክርስቶስ ትውልድ መጽሐፍ” ብሎ የጌታችንን የትውልድ ሐረግ በመዘርዘር ነው። ማቴ. 1፡1 ይህን በማድረጉ ግን ወንጌላዊውን ለምን ስለ ብስራት፣ ስለ ቀዳማዊነቱ “ቀዳሚሁ ቃል” ብሎ አልጀመረም? ተብሎ ይወቀሳልን? ወንጌላዊው ቅዱስ ማርቆስ ደግሞ ወንጌሉን የጀመረው “እነሆ፣ መንገድህን የሚጠርግ መልክተኛዬን በፊትህ እልካለሁ የጌታን መንገድ አዘጋጁ ጥርጊያውንም አቅኑ እያለ በምድረ በዳ የሚጮኽ ሰው ድምፅ ተብሎ በነቢዩ በኢሳይያስ እንደ ተጻፈ፣ ዮሐንስ በምድረ በዳ እያጠመቀ የንስሐንም ጥምቀት ለኃጢአት ስርየት እየሰበከ መጣ . . .” በማለት ስለ ጌታችን ልደትም ሆነ ስለ ብስራት ምንም ሳይል በቀጥታ የጀመረው ከጥምቀቱ ነው። ታዲያ ይህ ወንጌላዊውን የጌታን ብስራቱን፣ የዘር ሐረጉንንና ልደተን አይቀበልም ያሰኘዋልን? በጭራሽ! በኋላ በጊዜው ጊዜ ደግሞ መንፈስ ቅዱስ ዮሐንስ ወንጌላዊውን “ቀዳሚሁ ቃል” ብሎ እንዲጽፍ አደረገው። ሦስቱ ወንጌላውያን (ማቴዎስ፣ ማርቆስና ሉቃስ) በአብዛኛው ሰው የመሆኑን ነገር ትኩረት አድርገው መጻፋቸው አምላካዊነቱን መዘንጋታቸው አያሰኝም፣ ዮሐንስ ደግሞ አምላካዊነቱን ጎላ አድርጎ መጻፉ ሰውነቱን መዘንጋት አይባልም! አንድን አቅጣጫ ይዞ ብቻ መንጎድ እንደ ተወረወረ ቀስት አደገኛ ነው!

ቅዱስ ጰውሎስም በአቴና ከተማ ከግሪክ ፈላስፎች ጋር ባደረገው አስደናቂ ተዋስኦ ስለ ክርስትና አስተምህሮ በማስረዳት አልጀመረም። ይልቁንም ወደ ክርስትና ያቀርባቸው ዘንድ፣ ምንም እንኳ በከተማው ጣዖታት ሞልተው ማየቱ መንፈሱን በእጅጉ ረብሾት የነበረ ቢሆንም፣ “የአቴና ሰዎች ሆይ፣ እናንተ በሁሉ ነገር አማልክትን እጅግ እንደምትፈሩ እመለከታለሁ። የምታመልኩትን እየተመለከትሁ ሳልፍ፣ ለማይታወቅ አምላክ የሚል ጽሕፈት ያለበትን መሠዊያ ደግሞ አግኝቼአለሁና። እንግዲህ ይህን ሳታውቁ የምታመልኩትን እኔ እነግራችኋለሁ” በማለት ጀመረ። ከዚያም “ከእናንተ ከባለ ቅኔዎች አንዳንዶች ደግሞ፣ እኛ ደግሞ ዘመዶቹ ነንና ብለው እንደ ተናገሩ፣ በእርሱ ሕያዋን ነንና እንንቀሳቀሳለን እንኖርማለን” በማለት ከራሳቸው ፈላስፎችም ጠቀሰላቸው። የሐዋ. 17፡22-31 ይህ ግን ያስመሰግነዋል እንጂ እንዴት በቀጥታ ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ ከማስተማር አልጀመረም? ይህማ reductionism ነው አያሰኝም!

ስለሆነም በዘነበ ወላ ላይ የተጻፈችው ትንሽ ጽሑፍ ዋና ዓላማ ስለ ክርስትና “ሀሁ” ለማስተማር ወይም ስለ ምንኩስና ምንነት ፊደል ለማስቆጠር አይደለም። ሆኖም ምናኔያዊ ሕይወት መሠረቱና ዓላማው ቁሳዊ ሀብት ማከማቸትና በዚህ ዐለም መበልጸግ አለመሆኑ ሳይጠቀስ ግን አልታለፈም። ሆኖም የተነሣውን ጉዳይ ችላ ብሎ ባልተነሣ ጉዳይ ላይ ብዙ መድከም ዒላማውን የሳተ ስለሚሆን (ያልበላውን ማከክ እንደሚባለው)፣ በዚህም ላይ ገዳማት በሚባለው ጉዳይ ላይም ቢሆን የሚያኮራ ተጨባጭ ታሪክ የሌላቸው ስላልሆኑ፣ ይህ መብራራቱ “ከጥያቄዎቹ በላይ አደገኛ የሆኑት መልሶች” ሊያሰኝ ይችላልን? መድሎተ ጽድቅ ቅጽ ሦስት ላይ አንድ ምዕራፍ ተሰጥቶ ለመዳሰስ አልተሞከርምን? በፌስ ቡክ አጭር ጽሑፍ ላይ ያን ሁሉ ማብራራት ይጠበቅብኝ ነበረን?
ከላይ ለማንሣት እንደ ተሞከረው አንድን ጉዳይ በብዙ መንገድ ማብራራት ይቻላል። አባ ሶፍሮኒ የመለሱበት መንገድ በጣም ጥሩ ነው፤ ግን ብቸኛ መንገድ አይመስለኝም። አንዱ ይህን ሌላው ደግሞ ያንን አጽንኦት ቢሰጠው ይደጋገፋል፣ ሙሉ ይሆናል እንጂ እኔ ያልኩትን ካላሉ ወይም በእገሌ መንገድ ካልሆነ በሚል “ከጥያቆቹ በላይ አደገኛ የሆኑት መልሶች” እስከ ማለት መድረሱ አግባብነቱ አልታይህ ብሎኛል።
በዚህ አስተሳሰብ ከሄድን አንድ ሰው ስለ አንድ ጉዳይ ሁሉንም ነገር በአንድ ጊዜ ካልገለጸ በቀር፣ “ሌላ የሚያውቀው ግን ያልተናገረው ነገር የለም፣ ይህ ደግሞ ጎደሎነት ወይም reductionism ነው” ወደሚል ጽንፍ እንዳንሄድ ብናስብበት ጥሩ ነው። ይህ ጽሑፋችሁ ራሱ “ከመልሱ በላይ አደገኛ የሆነው መልስ” እንዳይሆን ብታስቡበት ጥሩ ነው።
ስለሆነም ለዘነበ ወላ በአጭሩ ለመስጠት የሞከርኩት መልስ እናንተ እንደምትሉት ገዳማዊ ሕይወትም ሆነ ክርስትና በኢኮኖሚያዊና መሰል ምድራዊ አስተዋጽኦዎቹ ይመዘን የሚል reductionist አይደለም፣ ወይም የገዳማዊ ሕይወትን መሠረታዊ ምነትና ዓላማ ለቁሳዊ መለኪያዎች አሳልፎ የሚሰጥ reductionist አይደለም። ፈጽሞ! ያልተባለውን የተባለ ለማስመሰል ከመድከም ይልቅ ሳይነቅፉ መጻፍ አይቻልም ይሆን? ምናልባት reductionism እንቃወማለን ስትሉ ሌላ ከባድ reductionist እንዳትሆኑ ብታስቡበት ጥሩ ይመስለኛል።
ቤተ ክርስቲያን ዐለሙ በሰፋላት ቀሚስ ውስጥ የመግባት ግዴታ የሌለባት መሆኑ አንድ መሠረታዊና ታላቅ ነገር ሆኖ፣ ዐለሙን መዋጀት ያለባት መሆኑ ደግሞ መዘንጋት የሌለበት ሌላው ጉዳይ ነው! ይህንስ ሌላው reductionism ነው እንበለውን? ጌታችን የተራቡትን እየመገበ የታመሙትን እየፈወሰ ያስተማረው ለምን ይሆን? ቤተ ክርስቲያን ይህ ዐለም የመሥሪያ ቦታዋ አይደለምን? ክርስትናስ ዐለሙን ለመዋጀት የሚችል አስተሳሰብ (ነጽሮተ ዐለም) እና አሠራር የሌለው ይመስል በሰዎች አኗኗርና እሳቤ ውስጥ ድርሻ የለውምን? ለምን ወደ ጓዳ እንዲደበቅ እናደርገዋለን? ለሰው ልጅ ሁለንተናዊ ሕይወት ከበቂ በላይ የሆነውን ክርስትና ለምን ከሙሉነቱ በጎደለ መንገድ እንዲታይ (ወይም እንደዚያ ለሚያስቡት) ግብዓት እንሰጣቸዋለን? በዚህ ዐለም ጉዳይ የማይመለከተው ነውን? ሌሎች እየመገቧቸውና እያለበሷቸው ያሉ ሰዎችን እኛ እናስተምራችሁ ብንላቸው ከልባቸው ይሰሙናልን? የሰዎች ረሃብና ችግርስ ቤተ ክርስቲያንን አይመለከታትምን? የተራቡና የተጠሙ ሰዎችስ ወንጌልን ለመስማት ምን ያህል ዝግጁ ናቸው ይሆን? ብዙ ነገሮችን ማንሣት ይቻላል። ግን ሐሳባችንን ስንገልጽ [እንደ ወንጌላውያን] በአንዱ አጽንዖት ያልተሰጠውን ጉዳይ ሳይነቅፉና ሳይፈርጁ የጎደለ እንኳ ቢኖር በሚሞላና በሚያንጽ መንገድ ቢሆን መልካም ይሆን ይመስለኛል! ለመነቃቀፍ የምናጠፋውን ጊዜ ሌላው ላይ ብናውለው እንዴት በተጠቀምን ነበር!
አሁንም ከሌላ reductionism ይሰውረን! ከዚህ በላይ አልበል!

Share...

Facebook
Telegram
WhatsApp
X
Email
Print
14 Comments
  • azahel
    azahel
    September 27, 2024 at 9:25 am

    ቃለህይወት ያሰማልን መምህራችን።በእውነቱ ከሆነ ገዳማት የቤተክርስቲያን የኢኮኖሚ የጀርባ አጥንት ይኾኑ ዘንድ ግድ የሚልበት ዘመን ላይ ነን።ገዳማት በልመና መነኮሳት በችግር የሚዋትቱበት ምክንያት ገዳማትን ከኢኮኖሚው ክበብ በማውጣታችን ነው።የግብፅ ገዳማት አቅማቸው የፈረጠመው በልመና አይደለም በምርትና አገልግሎታቸው በሚያገኙት አጥጋቢ ገቢ ነው።

    ያደላቸው monastic economy የተሰኘ ፍልስፍና ቀርጸውም ይንቀሳቀሳሉ።

    Reply
  • ኤርምያስ ተስፋኪሮስ
    ኤርምያስ ተስፋኪሮስ
    September 27, 2024 at 12:14 pm

    ጽሑፉን አንብቤዋለው ምን ቸገረኝ መሰላችሁ ሁለታችሁም በደንብ አንባቢ ናችሁ ብዬ አምናለው አውቃለውም ግን ምልከታዬን ለማስቀመጥ እይታ የምንመልስበት መንገድ ቢስተካከል ደስ ይለኛል( የትንሽ ወንድማችሁ ምልከታ ነው)።

    Reply
    • ቢኒያም
      ቢኒያም
      September 27, 2024 at 4:20 pm

      ተምረናል

      Reply
    • Kirubel Gezahegn
      Kirubel Gezahegn
      September 27, 2024 at 6:34 pm

      መምህር እግዚአብሔር ያክብርልን።በእውነቱ በዘነበ ወላ በተባለ ግለሰብ የተሰጠው ነቀፋዊ ሀሳብ የሚያተኩረው በስራ ላይ ነውና መነኮሳት ከስራ አንጻር ለዓለም የሰጡትን ወይም ያበረከቱትን ኢኮኖሚያዊ ጥቅም መግለጽ በመጣበት መመለስ እንጂ ይህ ብቻ ነው የምንኩስና ጥቅም ማለት አይደለምና።አንዳንዴ ሂስ የምንሰጥበትን ሁኔታ ከግምት እያስገባን እላለሁ።ወንድሞቻችን ላነሳችሁት ጥያቄ እግዚአብሔር ያክብራችሁ።

      Reply
    • ኤርምያስ
      ኤርምያስ
      September 29, 2024 at 8:07 pm

      የእኔ ስሜት ተመስገን ዋና ጠቀሰልኝ እግዚአብሔር ይስጥልኝ!

      Reply
      • Mengistu Mekebo
        Mengistu Mekebo
        October 8, 2024 at 3:35 am

        መምህር ያረጋል ቃለ ሕይወትን ያሰማልን በእውነት ቤተክርስቲያን በብዙ አይነት መንገድ ስታይ ወደ ፖለቲካ ውሰጥ ገብታለች። የተሰጠው ምላሸ ግን ፍቅር በተሞላ መንፈስ ስለሆነ ከሁሉ በላይ አእምሮን የሚቆጣጠር እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ለሁሉም ለቤተክርስቲያን ልጆቿ/ች ከፖለቲካ ወተው/ን ለተጠራንበት አለማ እንድንኖር ያድርግልን።

        በድጋሚ ቃለ ሕይወትን ያሰማልን በእድሜ በጤና ይጠብቅልን።

        Reply
  • EYOAB GIZAW
    EYOAB GIZAW
    September 27, 2024 at 1:49 pm

    መምህር ያረጋል አበጋዝም ሆነ በኤማሁስ ሕትመት የምታገለግሉ ወንድሞች ለቤተ ክርስቲያን ካላችሁ መልካም ቅንነት መሆኑን በጽኑ እገነዘባለሁና እግዚአብሔር በመንፈስቅዱስ ሀብት ይጠብቅልን እላለሁ። ነገር ግን መምህር ያረጋል በዳግም መልሳቸው ከሰጡት “በአንዱ አጽንዖት ያልተሰጠውን ጉዳይ ሳይነቅፉና ሳይፈርጁ የጎደለ እንኳ ቢኖር በሚሞላና በሚያንጽ መንገድ ቢሆን መልካም ይሆን ይመስለኛል! ለመነቃቀፍ የምናጠፋውን ጊዜ ሌላው ላይ ብናውለው እንዴት በተጠቀምን ነበር!
    አሁንም ከሌላ reductionism ይሰውረን!” እጋራለሁ።

    Reply
    • ብንያም
      ብንያም
      September 27, 2024 at 4:09 pm

      ቃለ ሕይወት ያሰማልን የጎደለውን መሙላት ይሻላል የጎደዳደውን እንደሞሉ አርገን እንቀበላቸው።
      በልኩ መተራረሙንም እንውደደው ።

      Reply
      • Workenh
        Workenh
        October 25, 2024 at 7:44 am

        Rock church of lalibela built b/n 7th _13 th centuries…and protestant reformation began in 1517. We ethiopian orthodox go earlier than the rest of world on cristanity. Google it. 🙏

        Reply
  • Jethro
    Jethro
    September 27, 2024 at 3:30 pm

    “አንዱ ይህን ሌላው ደግሞ ያንን አጽንኦት ቢሰጠው ይደጋገፋል፣ ሙሉ ይሆናል እንጂ እኔ ያልኩትን ካላሉ ወይም በእገሌ መንገድ ካልሆነ በሚል “ከጥያቆቹ በላይ አደገኛ የሆኑት መልሶች” እስከ ማለት መድረሱ አግባብነቱ አልታይህ ብሎኛል። ” መምህር ልቅም ያለ መልስ ሰጥተዋል ብዬ አምናለሁ፡፡
    ተዋሥኦ እንዲለመድ በመሻት ቢሆንም ቅሉ በአንዳንድ ርዕሰ ጉዳዮች ላይ ከምላስ ላይ ፀጉር ነቀላ የሚመስሉ ሀሳቦች የተነሱ ይመስለኛል፡፡ ብታስቡበት መልካም ነው። በተረፈ በርቱ ብዙ እየተማርኹ ነው።

    Reply
    • Melaku
      Melaku
      September 27, 2024 at 4:53 pm

      መምህራችን ቃለ ሕይወት ያሰማልን!
      የኤማሁስ ፕሬስ ሀሳቡን ማቅረባችሁ መልካም ነው ነገር ግን ጥያቂዎችን በመስጠትና በመመለስ ብዙ እየሰሩ ያሉ መምህራንን ጊዜ እየተሻማን ወደ ኋላ እንዳንጎትት የሚል ስጋት ሰሰላለኝ ነው
      “አሁንም ከሌላ reductionism ይሰውረን” እጋረዋለሁ

      Reply
    • እስጢፋኖስ
      እስጢፋኖስ
      September 27, 2024 at 7:06 pm

      መልካም ሀሣብ ነው መምህር እናንተም የምታነሱት ሀሣብ ጥሩ ነው ከዚህ በፊትም በሄኖክ ሀይሌ (በክርስቶስ ሁሉን እችላለሁ እና በአቡነ አረጋዊ ጽሁፍ) ሀሣብ ላይ Reductionism ተነስቶ ተመልክተናል በዚህም የ Reductionism ሀሣብ ከመለጠጡም በላይ ቤተክርስቲያንን ከአለም የማዉጣትና የምዕመናንን ማህበራዊ ና ኢኮኖሚያዊ ተሳትፎ የዘነጋ ይመስላል። ስለዚህም በአንድ Podcast ጽንሠ ሀሣቡን ብትዳስሱት መልካም ነው በተረፈ ብዙ እያስተማራችሁን ስለሆነ በዚሁ ቀጥሉ ሀሣብን በሀሣብ መሞገት ይልመድብን ከናንተ ብዙ እንጠብቃለን

      Reply
  • Yibeltal Y.
    Yibeltal Y.
    September 29, 2024 at 8:00 am

    ጊዜው የጦርነት እንጅ የልምምድ አይመስለኝም። ሁሉም ተባብሮ ቤተ ክርስቲያንን በሚወጋበት በዚህ ወቅት የራስህ ወገን አንተን ኢላማ ማድረግ ጤንነት አይመስለኝም። ለምሥጢርና ርቃቄው ከሰነበትን እንደርሳለን። መ/ር ያረጋል ምን ብሎ መመለስ ነበረበት? መፍትሔው አድርጎ ማሳዬት እንጅ ከማንም ቀድሞ በጥብአት መልስ የሰጠን የራስ ወገን መውጋት አይመስለኝም።

    Reply
  • Chere
    Chere
    October 14, 2024 at 2:08 pm

    It is well

    Reply
Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *

Related Posts

Emmaus Posts
በርናባስ ሽፈራው

“የአእላፋት ዝማሬ”

ሁለተኛው የአእላፋት ዝማሬ ባለፈው ዓመት በልደት ዋዜማ ተካሔደ ። በአዘጋጆቹ እና በተሳታፊዎቹ ዘንድ ይህ ሁለተኛው ዙር ከመጀመሪያው ዙር በላይ ያማረ እና የሠመረ ሆኖ ተቆጥሯል ። በጠቅላላው ከምእመናን በኩል በተሳትፎም ሆነ በማኅበራዊ ሚዲያ ያገኘው ተቀባይነት ሌሎች ሁነቶች ሲሆኑ እንደምናየው በጅምር የሚቀር ሳይሆን እንደ ባህል የመተከል ዕድሉ ሰፊ መሆኑን ያመላክታል ። እንዲያውም በአዲስ አበባ እና በድሬዳዋ ብቻ ሳይወሰን ወደ ሌሎች ቦታዎችም እንዲሰፋ የሕዝብ ጥያቄ እና በአዘጋጆቹም በኩል እቅድ መኖሩ ይታወቃል ። ስለዚህ በጥቂት ዓመታት ውስጥ ልክ እንደ ጥምቀት ሁሉ በሁሉም ዋና ዋና ከተሞች ውስጥ (የአዘጋጆቹ አቅም በፈቀደው ልክ) የአእላፋት ዝማሬ የልደት በዓል መለያ ሆኖ እንዲካሔድ መጠበቅ እንችላለን ። ይህ ነገር በብዙዎች ዘንድ ለቤተ ክርስቲያን ታላቅ ጥቅም የሚሰጥ ሆኖ ይታያል ። በእነርሱ ዐይን ይህ ሁነት ቤተ ክርስቲያን በብዙዎች ዘንድ እንድትታወቅ ያደርጋል ። ብዙዎች በዓሉን አስመልክተው ከሚሔዱባቸው የማይገቡ ዓውዶች ወደ ቤተ ክርስቲያን እንዲመለሱ ከማድረጉ ባሻገር ፥ በቤተ ክርስቲያን ሱታፌ ያላቸውንም በሚስብ እና በሚገባቸው መልኩ ቤተ ክርስቲያንን የበለጠ እንዲያውቋት ያስችላቸዋል ። ስለዚህም የሌሉትን በመጥራት ፥ ያሉትንም በማጽናት ቤተ ክርስቲያን ዘመኑን እንድትዋጅ የሚያስችላት መሣሪያ ነው ፤ ከእርሷ ዘንድ ወደ ክሕደት እና ወደ ኑፋቄ የፈለሰውን ፥ ወይም በስም ክርስቲያን ሆኖ እና ማዕተብ አስሮ ሳለ በምድራዊ ተድላ ባሕር የሰጠመውን ወጣት ወደ ራሷ የምትስብበት መረብ ነው ። ነገር ግን ከኖረው የቤተ ክርስቲያን ትውፊትና አስተምህሮ አንጻር ከመረመርነው ፥ ይህ ሁነት

Read More »
Emmaus Posts
ኤልያስ ገብረ ሥላሴ

መከራ ፣ እከይ እና ክርስትና

መከራ በክርስቲያኖች ሕይወት ውስጥ ድንገተኛ የሆነ ክስተት አይደለም ። ፍቅር በሆነው እግዚአብሔር ለጥቅማችን የሚፈቀድ የእርምት መንገድ ነው እንጂ ። በየዘመኑ ቤተክርስቲያን በወቅታዊ ሁነቶች እንድትወጠር እና መሠረታዊ ነገሮች ትኩረት እንዳያገኙ የሚቀርብ ፈተና አለ ። ሰበር ዜናዎች ፣ ወቅታዊ አጀንዳዎች ፣ አከራካሪ ጉዳዮች ወዘተ ከመነኩሴ መቁጠሪያ በላይ በሚሽከረከሩበት ዘመን ላይ ነው የምንገኘው ። እነዚህ ሁነቶች ትኩረታችንን ይወስዱትና ሳይታወቀን መሠረታዊ ከሆኑትና ዘለዓለማዊነታችንን ከሚበይኑት ጉዳዮች ወጥተን ምድራዊና እዚሁ ቀሪ በሆኑ ጉዳዮች ተወጥረን እንገኛለን ። እጅግ የሚያሳዝነው ደግሞ ይህ ሁኔታ በቤተክርስቲያንን መምህራን እና “ተጽዕኖ ፈጣሪዎች” ላይ እጅግ በርትቶ የሚታይ መሆኑ እና በቤተክርስቲያን ዐውደ ምሕረት እና መድረኮች ሳይቀር ሰፊውን ሰዓት መያዙ ነው ። የቤተክርስቲያን ተልእኮ ስለ ክርስቶስ ምስክር መሆን ነው ። መሠረታዊ ካልሆኑት ሁነቶች ወጥተን ወደዚህ ዋነኛ ተልእኮአችን እንድንመለስ ተዋሥኦ ትልቅ ሚና ይኖረዋል ። ይህ በምእመናን ፥ በተለይ ደግሞ በቤተክርስቲን አገልጋዮች ፥ ዘንድ እጅግ አስፈላጊ የሆነ ነገር ነው ። የሁነቶችን መሠረት መመርመርና ትክክለኛ ባሕርያቸውን መረዳት ያሻል ። ሁነቶቹ ችግሮች የሆኑ እንደሆነ ሥር ነቀል መፍትሔ ማሰብ የሚቻለው ፥ መልካም አጋጣሚዎችም ከሆኑ በትክክለኛው መንገድ ጥቅም ላይ ልናውላቸው የምንችለው የሁነቶቹን መሠረት በጥልቀት መረዳት ከቻልን ነው ። በመቀጠልም ተከትለው ሊደረጉ ስለሚገቡ ነገሮች መወያየት ከተቻለ ብቻ ነው ። ካልሆነ አሁን እየሆነ እንዳለው የወቅታዊ አጀንዳዎች አሳዳጅ ብቻ ሆነን ነው የምንቀረው ። በተለይ ዘመናችን የማኅበራዊ ሚዲያ ተጽዕኖ ከፍተኛ ደረጃ ላይ የደረሰበት ስለሆነ በዚህ

Read More »
Emmaus Posts
መሐሪ ዘመልአክ

ከእውነት አልባነት ጋር የሚካሔድ ሙግት

(‘ሐሳቦች መዘዝ አላቸው’ በሚል ርእስ በኤማሁስ መጽሔት ቅጽ 1 ፣ ቁጥር 1 በወጣው ጽሑፍ ላይ የተጻፈ አስተያየት) በመሐሪ ዘመልአክ (PhD) ከዛሬ አሥራ አምስት ዓመታት በፊት የእጓለ ገብረ ዮሐንስ ‘የከፍተኛ ትምህርት ዘይቤ’ ለመጀመሪያ ጊዜ ካነበብኹ በኋላ ጸሐፊውን ከዚያ በፊት አለማወቄ ገርሞኝ እንደነበር አስታውሳለኹ ። ማን ናቸው ? እንዴት እስከዛሬ ድረስ ስለእርሳቸው ሳልሰማ ቀረኹ ? ለምን ? ይኼ በ1956 ዓ.ም. የታተመ የሬድዮ ንግግር ከኾነ መጽሐፍ ለመጻፍ ብለው ተነሥተው ቢጽፉ ኖሮ ምን ሊጽፉ ነበረ ? ወዘተ. የሚሉ ጥያቄዎች ጭንቅላቴ ውስጥ ተመላልሰዋል ።[1] በኋላ ፈላስፋው ኦርቶዶክሳዊ አማኝ ፣ የኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ተማሪና መምህር እንደነበሩ ስሰማ በመጽሐፉ ውስጥ ያየሁት የሐሳብ ጥልቀት በዘመኑ በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ልሒቃን ዘንድ የነበረው ተዋሥኦ ሊደርስ ይንጠራራበት የነበረውን ልክ የጠቆመኝ መሰለኝ ። ከዚያ በኋላ ያ የተዋሥኦ ልሕቀት የት ገባ ? እንዴት ድርቅና የተጫነው ተዋሥኦ ዋጠው ? እንዴት ኦርቶዶክሳዊነትን ከአመክንዮ የተፋታ እና አመክንዮን የሚፈራ ጭፍን እምነት የሚያስመስሉ የፎክሎር ሰባኪዎች ተፈለፈሉብን ?  የኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ካህን ለመኾን የሚጠየቀው መስፈርት ስለምን ድፍረት የለበሰ አላዋቂነት መሰለ ? በሚዲያ ላይ ሲናገሩ በአላዋቂነታቸው አንገታችንን የማያስደፉን ካህናት ስለምን ቁጥራቸው አልበረክት አለን ? ኦርቶዶክሳዊነት ችግርን እና ጭንቀትን ለማረሳሳት የተጠመቀ ዕፀ-ዝንጋዔ (‘opium of the masses’) እስኪመስል ድረስ በኦርቶዶክሳዊነት ስም የገነነው ተዋሥኦ ለምን አላዋቂነት ተጫነው ? ቤተ ክርስቲያን ሲባል ከስሜታዊ ሙጥኝታ (sentimental attachment) ባለፈ ለሰው ልጅ ህልውናዊ ጥያቄ የተሰጠ ከሞት ፍርኃት

Read More »
Emmaus Posts
ኤማሁስ

የኤማሁስ መንገድ

መጽሔቷን ለማግኘት ይህን ይጫኑ . . . የዘመናችን ተዋሥኦ በይዘቱም ሆነ በመንገዶቹ በግልብነት በእጅጉ የተጠቃ ነው ። ‘በይዘቱ እንዴት ?’ቢባል ሁነቶች ላይ ያተኮረ እና ወቅታዊነትን ማዕከል ያደረገ በመሆኑ ። አንድም አቋም ከመያዝና ጎራ ከፍሎ ከመናቆር ባለፈ የእውነት የመማር እና የማሰላሰል ጉጉት የማይታይበት በመሆኑ ። በዚህ ተዋሥኦ ውስጥ መሠረታዊ ጥያቄዎችን ማንሣት እና ከሁነቶቹ የሚሻገር እና ሐሳባዊ የሆነ ትንተና ለማካሔድ መሞከር ትኩረት ያስነሣል ፤ ሲብስም አጉል እንደመራቀቅ ይታያል ። የሚካሄድበት ከባቢ እና ዘመን ደግሞ ሌላ ግልብነት ደርቦለታል ። በእኛ ሀገር ብቻ ሳይሆን በሌሎችም ሀገራት ፣ ከዘመናዊነትና ከቴክኖሎጂ መራቀቅ ጋር ተያይዞ ሕዝባዊ ተዋሥኦ በጠቅላላው ስለቱን እና ርቀቱን እንዲያጣ ሆኗል ። የሚነበብም ሆነ የሚታይ ወይም የሚደመጥ ነገር አጭር መሆን አለበት ። ነገር ግን ጠቃሚና ወሳኝ ርእሶች እንዲህ ባለ መንገድ ሊስተናገዱ አይችሉም ። የሚያጠግብ ፍሬ ከሌለበት የተመልካቹ እና የአንባቢው ብዛት ምን ጥቅም ይኖረዋል ? እንዲህ ባለው ከባቢ ውስጥ ሁነቶችን ከሁነትነታቸው እና ከሚያመጡት ወቅታዊ ውጤት በተሻገረ መልኩ ለመመልከት እንቸገራለን ። ቀድሞውኑም (እይታችን ከመጥበቡ የተነሣ) ጠባብ አድርገን የቀረጽነውን አጀንዳ በምንገልጽበት መንገድ የበለጠ እናጠብበዋለን ። ነገር ግን ሁነቶችን እና ሒደቶችን ከመሠረታቸው መመርመራችን እና የምናቀርባቸው መፍትሔዎችም እንዲሁ የማይናወጥ መሠረት ያላቸው መሆናቸው አስፈላጊ ከሆነ ተዋሥኦውም እንዲሁ የጠለቀ እና የረቀቀ መሆን አለበት ። ይህን ለማድረግ ደግሞ ጊዜ ወስዶ ማሰብ ፣ ማንበብ ፣ ማጠናቀር ፣ መወያየት ፣ መሟገት እና እንዲህ ካለው ሒደት

Read More »
Emmaus Posts
በርናባስ ሽፈራው

ክፍል ፭ ፡ ወደ ርስታችን ያልተመለስንበት ኢዮቤልዩ

ሩሲያዊው ደራሲ ፌዮዶር ዶስቶየቭስኪ በ1860ዎቹ አውሮፓን ለመጀመሪያ ጊዜ ሲጎበኝ የታዘበውን በዘገበበት ማስታወሻው የለንደን ድሆች ቅዳሜ ማታን እንዴት ባለ መንገድ እንደሚያሳልፉ ይነግረናል ። በቅድሚያ ሌሊቱን በሙሉ ወንዶች ብቻ ሳይሆኑ ሚስቶቻቸውና ልጆቻቸው ጭምር ደስታ ፈጽሞ በተለየው ፣ ድብርት በተጫነው መንፈስ አኳዃን ሲበሉ እና ሲጠጡ ፣ ከሕይወታቸው መራራነት ለማምለጥ ፣ ራሳቸውን ፍጹም ለማደንዘዝ በሙሉ ጥምብዝ እስኪሉ እንደሚሰክሩ መስማቱን ይዘግባል ። ሳምንቱን ሙሉ ሠርተው የቋጠሯትን ገንዘብ ቅዳሜ ሌሊት እንዲህ ይበትኗታል ። አስከትሎም እንዲህ ባለው አንድ ምሽት እሱ ራሱ በመንደራቸው ውስጥ ሲያልፍ የታዘበውን እና የተሰማውን እንደሚከተለው ይመሰክራል ። “One such night – it was getting on for two o’clock in the morning – I lost my way and for a long time trudged the streets in the midst of a vast crowd of gloomy people, asking my way almost by gestures, because I do not know a word of English. I found my way, but the impression of what I had seen tormented me for three days afterwards. The populace is much the same anywhere, but there all was so vast, so vivid that you almost physically felt things which up till then you had only imagined. In London, you no longer see the populace. Instead, you see a loss of sensibility, systematic, resigned and

Read More »
Emmaus Posts
በርናባስ ሽፈራው

ብያኔን አሳልፎ ያለመስጠት ግዴታ

ከሁለት ሳምንታት በፊት ‘ከጥያቄዎቹ በላይ አደገኛ የሆኑት መልሶች’ በሚል ርእስ አንድ ጽሑፍ አቅርበን ነበር ። ጽሑፉ በዋናነት ማሳነስ (reductionism) የተባለውን ፅንሰ ሐሳብ የሚያነሣ እና የሚተች ነው ። በዚህ ጽሑፋችን ውስጥ መምህር ያረጋል አበጋዝ በቅርቡ ‘ወደ ላይ አያዳልጣችሁ’ በሚል ርእስ ገዳማዊ ሕይወትን ከዘነበ ወላ ዘለፋ ለመከላከል ጽፎ ያጋራውን ጽሑፍ ተችተናል ። ርእሱን በዚህ ጊዜ ጉዳይ ያደረግነውም በዋናነት በምምህር ያረጋል ጽሑፍ ምክንያት ነው ። በተለይ ጽሑፉ ሰፊ ተነባቢነት እና ተቀባይነት ያገኘ እንደ መሆኑ በውስጡ ያየነውን የማሳነስ ዝንባሌ መተቸቱ ጠቃሚ ይሆናል ብለን አመንን ። ነገር ግን የመምህር ያረጋል ጽሑፍ መነሻ ቢሆነንም በይበልጥ ፅንሰ ሐሳቡ ላይ ለማተኮር ነው የሞከርነው – ዓላማችን ነገሩ ላይ ተዋሥኦ እንዲጀመርና የተሻለ መረዳት እንዲፈጠር ማድረግ ስለሆነ ። መምህር ያረጋልም ጽሑፉን ተመልክቶ ምላሽ ሰጥቶናል ። ምላሽ በመስጠቱ ደስ ብሎናል ። በምላሹ ግን አልተደሰትንም ። አለመደሰታችን እኛ በእርሱ ጽሑፍ ላይ ያቀረብነውን ትችት ባለመቀበሉ አይደለም ። ይልቁንም የተሰጠው ምላሽ ከእኛ ትችት ጋር እምብዛም የተያያዘ ባለመሆኑ እንጂ ። ከነገሩ ጋር የማይገጥሙ ምሳሌዎች ቀርበዋል ። ያቀረብነው ሂስ በተሳሳተ መንገድ ተተርጉሟል ። በጽሑፋችን በስም ጠርተን ያራቅነው እና ያነወርነው ሐሳብ የእኛ አቋም ተደርጎ ተገልጧል ። “ለቤተ ክርስቲያን ከልባችን ከመጨነቅና ከመቅናት” ተነሥተን “ያልተባለውን ለማስመሰል በመድከማችን” ተወቅሰናል ፤ ዕጣችን ሆኖ “ሳንነቅፍ መጻፍ አልቻልንምና” ። እነዚህ ሁሉ ነገሮች መልስ እና እርማት የሚሹ ሆነው አግኝተናቸዋል ። አንድም ለእኛም ሆነ ለመምህር ያረጋል

Read More »