መከራ ፣ እከይ እና ክርስትና

መከራ በክርስቲያኖች ሕይወት ውስጥ ድንገተኛ የሆነ ክስተት አይደለም ። ፍቅር በሆነው እግዚአብሔር ለጥቅማችን የሚፈቀድ የእርምት መንገድ ነው እንጂ ። በየዘመኑ ቤተክርስቲያን በወቅታዊ ሁነቶች እንድትወጠር እና መሠረታዊ ነገሮች ትኩረት እንዳያገኙ የሚቀርብ ፈተና አለ ። ሰበር ዜናዎች ፣ ወቅታዊ አጀንዳዎች ፣ አከራካሪ ጉዳዮች ወዘተ ከመነኩሴ መቁጠሪያ በላይ በሚሽከረከሩበት ዘመን ላይ ነው የምንገኘው ። እነዚህ ሁነቶች ትኩረታችንን ይወስዱትና ሳይታወቀን መሠረታዊ ከሆኑትና ዘለዓለማዊነታችንን ከሚበይኑት ጉዳዮች ወጥተን ምድራዊና እዚሁ ቀሪ በሆኑ ጉዳዮች ተወጥረን እንገኛለን ። እጅግ የሚያሳዝነው ደግሞ ይህ ሁኔታ በቤተክርስቲያንን መምህራን እና “ተጽዕኖ ፈጣሪዎች” ላይ እጅግ በርትቶ የሚታይ መሆኑ እና በቤተክርስቲያን ዐውደ ምሕረት እና መድረኮች ሳይቀር ሰፊውን ሰዓት መያዙ ነው ።

የቤተክርስቲያን ተልእኮ ስለ ክርስቶስ ምስክር መሆን ነው ። መሠረታዊ ካልሆኑት ሁነቶች ወጥተን ወደዚህ ዋነኛ ተልእኮአችን እንድንመለስ ተዋሥኦ ትልቅ ሚና ይኖረዋል ። ይህ በምእመናን ፥ በተለይ ደግሞ በቤተክርስቲን አገልጋዮች ፥ ዘንድ እጅግ አስፈላጊ የሆነ ነገር ነው ። የሁነቶችን መሠረት መመርመርና ትክክለኛ ባሕርያቸውን መረዳት ያሻል ። ሁነቶቹ ችግሮች የሆኑ እንደሆነ ሥር ነቀል መፍትሔ ማሰብ የሚቻለው ፥ መልካም አጋጣሚዎችም ከሆኑ በትክክለኛው መንገድ ጥቅም ላይ ልናውላቸው የምንችለው የሁነቶቹን መሠረት በጥልቀት መረዳት ከቻልን ነው ። በመቀጠልም ተከትለው ሊደረጉ ስለሚገቡ ነገሮች መወያየት ከተቻለ ብቻ ነው ። ካልሆነ አሁን እየሆነ እንዳለው የወቅታዊ አጀንዳዎች አሳዳጅ ብቻ ሆነን ነው የምንቀረው ።

በተለይ ዘመናችን የማኅበራዊ ሚዲያ ተጽዕኖ ከፍተኛ ደረጃ ላይ የደረሰበት ስለሆነ በዚህ መደላድል ላይ እየተስተዋሉ ያሉ ሁነት ተኮር ልጥፎች ፣ ውይይቶችና ክርክሮች ወደ መሠረታዊ ነገሮች እንዲያተኩሩ እና በቶሎ ፈር እንዲይዙ ካልተደረገ በብዙኃኑ ዘንድ ቤተክርስቲያን ተልዕኮዋ ከዚህ የዘለለ እንዳልሆነ ተደርጋ እንድትታሰብ እና ሰማያዊነቷ እንዲዘነጋ ያደርጋል ። በዚህ ረገድ ኤማሁስ ፖድካስት እና መጽሔት ፈር ቀዳጅ ሆነው ብቅ ብለዋል ። በዚህ አጋጣሚ ኤማሁስ ፖድካስትና መጽሔትን እንድትከታተሉ ለሌሎችም እንድታጋሩ እጋብዛለሁ ።

መጽሐፍ ቅዱስ ላይ ጥያቄ የሚፈጥሩብን ፣ ለመረዳት የሚያስቸግሩንና ስለ እግዚአብሔር መልካምነት ካለን ዕውቀት ጋር የሚጋጩ የሚመስሉ አንዳንድ ጥቅሶች አሉ ። “ብርሃንን ሠራሁ ፤ ጨለማውን ፈጠርሁ ። ደኅንነትን እሠራለሁ ፤ ክፋትንም እፈጥራለሁ ። እነዚህን ሁሉ ያደረግሁ እኔ እግዚአብሔር ነኝ ።” የሚለው በትንቢተ ኢሳይያስ ያለው ኃይለ ቃል ከነዚህ ጥቅሶች ውስጥ አንዱ ነው ። “ክፋትን እፈጥራለሁ” በሚለው መጣጥፉ ወንድማችን ብንያም የዚህን ከባድ ጥቅስ ትርጉም በቤተክርስቲያን ህያው በሆነው የአባቶች ትምህርት በኩል እንድንረዳው ይጋብዘናል ። ጽሑፉ የጥቅሱን ትርጉም በማስረዳት ውስጥ ስለ መልካም (በጎ) ፣ ክፋት (እከይ) እና መለኮታዊ መግቦት (Divine providence) በቤተክርስቲያን አባቶች ትምህርት መነሻነት ጥልቅ የሆነ ነገረ መለኮታዊ ትንተና የተሰጠበት ነው ። በየዘመኑ አማኞች  ‘ክፋት ከየት መጣ ? እግዚአብሔር ለምን ይፈቅደዋል ? ከእግዚአብሔር መልካምነትስ ጋር እንዴት አብሮ ይሄዳል ?’ በሚሉና በመሰል ጥያቄዎች ይፈተናሉ ። ይህ መጣጥፍ ለነዚህ ጥያቄዎች አጥጋቢ መልስ የተሰጠበት ነው ።

ጽሑፉ የሚጀምረው ክፋት እንደ ተመልካቹ ነው የሚለውን የሞራላዊ (ግብረ ገብ) አንጻራዊነትን (Moral Relativism) ዕሳቤ ስሕተትነት በጥቂቱ በመጠቆም ነው ። ይህንን ዕሳቤ ከሚያንጸባርቀው ‘ክፋትን ስናየው እናውቀዋለን’ ከሚለው አባባል በመነሣት አንባቢውን ከግላዊ የሞራል (Moral Subjectivism) አረዳድ አውጥቶ ወደ ገሀዳዊ የሞራል (Moral Objectivism) አረዳድ ይወስደዋል ። በዚህም ጉዳዩን ከግላዊ አተያይ (Personal Opinion) በማሻገር መልካምን መልካም፤ ክፉንም ክፉ የሚያሰኙት ወይም የሚያደርጉት ነገሮች ምንድናቸው? የሚለውን መሠረታዊ ጥያቄ ይመልሳል ። የፈጠረው ነገር ሁሉ መልካም እንደሆነ የተመለከተ እግዚአብሔር “ክፋትን እፈጥራለሁ” ሲል ምን ማለቱ ነው? የሚለውን ለመረዳት ይህንን መሠረታዊ ጥያቄ መመለስ የግድ ነው ። ብንያም ይህንን የሚያደርገው ፈላስፋው ሶቅራጥስ ዩቲፍሮ ለሚባል ወዳጁ ያቀረበለትን ጥያቄ መነሻ በማድረግ ሞራል (ግብረ ገብ) የእግዚአብሔር ፈቃድ ላይ የተመሠረተ ነገር ነው ? ወይስ ከእግዚአብሔር ውጪ ያለ በራሱ ቀዋሚ የሆነ ነገር ነው? የሚል ጥያቄ በማንሣት እና የዚህን ጥያቄ ምላሽ በማብራራት ነው ።

የመጣጥፉ ጠንካራ ጎን ይህን ጥያቄ የቤተክርስቲያን አባቶች እንዲመልሱት ማድረጉ ነው ። ብንያም ለዚህ መሠረታዊ ጥያቄ ምላሽ ፍለጋ የተጓዘው ወደ ቀደሙ አባቶች ወደነ ቅዱስ ጎርጎርዮስ ዘኑሲስ ፣ ዲዮናስዮስ ፣ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ እና ከቅርብ ዘመን የነገረ መለኮት ሊቃውንት ወደነ ዱሚትሩ ስታኒሎይ ፣ ክርስቶስ ያናራስ ፣ ጆርጀስ ፍሎሮቭስኪ እና ዴቪድ ቤንትሌይ ሀርት ነው ። በዚህም ኦርቶዶክሳዊነት ‘በከመ መሀሩነ አበው – አባቶች እዳስተማሩን’ ማለት እንደመሆኑ አባቶችን እንዲሁ ለመጥቀስ ያህል ሳይሆን እያንዳንዱ የተጠቀሰው ትምህርታቸው ጽሑፉን አንድ እርምጃ እያስጓዘ በስተመጨረሻም ልክ (Sound) ወደ ሆነው የጽሑፉ መነሻ ጥቅስ መረዳት የሚያደርስ ነው ። በአጭሩ ጽሑፉ መነሻ እና መድረሻ ያደረገው የቤተክርስቲያን አባቶችን ነው ።

የመጣጥፉ የጀርባ አጥንት ቅዱስ ጎርጎርዮስ ስለ ክፋት ምንነት ያስተማረው ትምህርት ነው ። እንደ ቅዱስ ጎርጎርዮስ አስተምህሮ ክፋት የበጎነት አለመኖር ወይም መታጣት ሲሆን ክፋት በራሱ ህላዌ ወይም ምንነት የሌለው ነው ። ስለዚህ ክፋት በእግዚአብሔር የተፈጠረ ሳይሆን የበጎነት ወይም መልካምነት አለመኖር ነው ። ከዚህ በመነሣት ብንያም ክፋት የምንለው ፍጡር ለባሕርይው የማይስማማ እንቅስቃሴ ማድረጉን መሆኑን ያወሳል ። የዲዮናስዮስ ዐሳብም ተጠቅልሎ ክፋት በራሱ ህልው ያልሆነ ነገር ግን ጥገኛ በመሆን ሰውነትን በሚጎዳ በሽታ ተመስሎ ቀርቧል ። ፍሎሮቭስኪም ክፋት ነጻ ፈቃድ ያላቸው ፍጥረቶች (መላእክት እና ሰዎች) በምርጫቸው ከእግዚአብሔር መቃረናቸው የሚያመጣው ውጤት ነው በማለት ይህንኑ ዐሳብ  ያጠናክረዋል ። “ክፋት የመንፈስ ክሂላት ወደተሰጣቸው መዳረሻ ያይደለ ወደ ሌላ ነገር የሚያደርጉት ኢ ምክንያታዊ እንቅስቃሴ ነው” የሚለው የስታኒሎይ አረዳድ ደግሞ የጽሑፉን ጠቅላላ ዐሳብ ከነጻነት እና ሐላፊነት ጎዳና አንጻር የሚያስር ነው ። ምክንያቱም ሰው የመረጠውን እንቅስቃሴ የማድረግ ነጻነት እንዳለው ሁሉ ፥ ላደረገው እንቅስቃሴም ሓላፊነትን የመውሰድ ግዴታ አለበትና ነው ። በነጻነቱ መርጦ ለተፈጥሮው የማይስማማ ኢ-ምክንያታዊ እንቅስቃሴ ባደረገ ቁጥር ክፋት ይወለዳል ፤ የዚህም ክፋት ባለቤትነት (ሐላፊነት) ደግሞ የራሱ ነው ። በአጠቃላይ መልካም ወይም በጎ የምንለው ከእግዚአብሔር የተገኘውን እና የእርሱ ፈቃድ የሆነውን ነገር ሁሉ ነው ። ክፋት ደግሞ የዚህ ተቃራኒ ነው ። ስለዚህ የክፋት ምንጩ ኃጢአት ነው ፤ ምክንያቱም ኃጢአት ከእግዚአብሔር መቃረን ነውና ።

ብንያም በመቀጠል ‘በሞራላዊ እኩይ’ እና ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ‘እኩይ ሊባሉ የማይገባቸው ፥ ነገር ግን እኩይ የምንላቸው’ በሚላቸው ነገሮች መካከል ያለውን ልዩነት በጥንቃቄ ያስረዳል ። ቅዱሱ እኩይ ሊባሉ የሚገባቸው የሚለው ሞራላዊ የሆኑትን እንደ ዝሙት እና ፍቅረ ንዋይ ያሉ ነገሮችን ሲሆን ፤ እኩይ ሊባሉ የማይገባቸው ነገር ግን እንደዛ እያልን የምንጠራቸው የሚላቸው ደግሞ እንደ ረኃብ ፣ ወረርሽኝ ፣ ሞት ፣ በሽታ ያሉትን ነው ። ብንያም ቅዱሱን መነሻ በማድረግ መጽሐፍ ቅዱስ በአንዳንድ ቦታ እነዚህን እኩይ ሊባሉ የማይገባቸው ነገሮች እኩይ ሲላቸው ቢገኝም በሞራላዊ ዐውድ ማለቱ አይደለም ይለናል ። በኢሳይያስ ትንቢትም ቃሉ ጥቅም ላይ የዋለው በዚሁ አግባብ ነው ። ለዚህም በተመሳሳይ መንገድ ያቀረበው አመክንዮ ‘እነዚህ ነገሮች ክፉ (እኩይ) ቢሆኑ ኖሮ ትዕቢታችንን በመገሠፅ ፣ ስንፍናችንን በማባረር ወደ መነሣሣት እየመሩን እና ትኩረታችንን ወደ ሚገባው ቦታ እየሳቡልን የመልካም ነገር መገኛ ባልሆኑልን ነበር ።’ የሚል ነው ። ይህ እጅግ መሠረታዊ የሆነ ጉዳይ ነው ። ምክንያቱም እግዚአብሔር ክፋትን እንዳልፈጠረ ከማስረገጡ በተጨማሪ ክፉ ሳይሆኑ ክፉ እያልን በምንጠራቸው ነገር ግን የእግዚአብሔር የመግቦቱ መገለጫ በሆኑ ነገሮች እና ክፉ የሚለው መጠሪያ በሚገባው በሞራላዊ ክፋት መካከል ያለውን ልዩነት ቁልጭ አድርጎ ስለሚያሳይ ነው ።

ተሰናስሎውን በጠበቀ መንገድ ይህንን መደላድል ከፈጠረ በኋላ ነው ብንያም የተነሣበትን የኢሳይያስን ትንቢት ቃል ወደ ማብራራት የሚገባው ። እግዚአብሔር “ክፋትን እፈጥራለሁ” ሲል ክፋት የተባለው ሞራላዊ እኩይ ሳይሆን የመግቦቱ አካል የሆነው መቅሰፍት ነው ። ለዚህም ማሳያ እንዲሆን የአይሁድ ሊቃውንት ይህንን የትንቢት ክፍል ሲተረጉሙ ጨለማን ‘የብርሃን አለመኖር’ ፥ ክፋትንም ‘የሰላም አለመኖር’ ብለው እንደፈቱት ያነሣል ። ስለዚህ ‘ክፋትን እፈጥራለሁ’ ማለቱ (የሰላም አለመኖር) በፋርስና በባቢሎን መካከል ጦርነት አመጣለሁ ማለቱ ሲሆን ‹ደኅንነትን እሠራለሁ› ማለቱ ደግሞ የፋርሱን ንጉሥ ቂሮስን እንደሚያበረታው መናገሩ ነው ብለው መተርጎማቸውን ያነሣል ። ቅን ለሆኑት ብርሃንን ለክፉዎች ደግሞ ጨለማን እንደሚከፍል በማውሳት ለዚህ ማሳያ በቅዳሴ ማርያም ኅብስቱ እና ወይኑ እንደተቀባዮቹ ሁኔታ ውጤቱ የተለያየ መሆኑ የተገለጠበትን ከፍለ ንባብ ያነሣል ። ከዚህ በመቀጠል ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅን መነሻ በማድረግ በኢሳይያስ ትንቢት ክፋት የተባለው ከሰው ፈቃድ የሚመነጨው ክፋት ሳይሆን እግዚአብሔር ከመግቦት የተነሣ ለእርምት ወይም ለማስተማሪያነት የሚያመጣቸው መቅሰፍቶችን መሆኑን እና የጥቅሱ ትርጉምም ይኸው መሆኑን ያስረግጣል ።

ብንያም ጽሑፉን የሚጠቀልለው ይህንን ከላይ ያብራራውን እውነት በተግባር የቀመሰውን ጻድቁን ኢዮብን በማንሣት ነው ።ኢዮብ ከሰይጣን በሆኑ ብዙ ፈተናዎች ተፈትኗል ። እነዚህ ፈተናዎች ከሰይጣን ይሁኑ እንጂ ኢዮብ ይፈተንባቸው ዘንድ እግዚአብሔር ፈቃዱን የሰጠባቸው ናቸው ። ይህም የኢዮብ እምነት ይፈተን ዘንድ ነው ። ስለዚህ እግዚአብሔር ከመግቦቱ የተነሣ ኢዮብን በፈተና ውስጥ ሊያስተምረው ይፈተንባቸው ዘንድ ፈቃዱን የሰጠባቸው መቅሰፍቶች ናቸው ። እነዚህ በራሳቸው ክፉ አይደሉም ፤ ምክንያቱም ኢዮብ ቢያገኝም ቢያጣም በጽድቅ ሕይወት መጽናት እንዳለበት ይማርበት ዘንድ የመጡ ፈተናዎች ናቸውና ። ክፋት ይመነጭ የነበረው ኢዮብ በፈተናው ወድቆ እግዚአብሔርን ቢበድል ፤ ኃጢአት ቢሠራ ነበር ። ምክንያቱም የክፋት ምንጩ ኃጢአት ነውና ። ስለዚህ ጥቅሱ ላይ እግዚአብሔር እፈጥረዋለሁ ያለው ክፋት ሞራላዊ የሆነውን እና ነጻ ፈቃድ ካላቸው ፍጥረታት የሚመነጨውን ክፋት ሳይሆን ከመግቦቱ ስለ ጥቅማችን የሚያመጣቸው መቅሰፍቶችን ነው ።

መጣጥፉ መነሻው ላደረገው ጥቅስ ምላሽ ከመስጠትም በዘለለ ኦርቶዶክሳዊ ነገረ ሰብእን (ሰው የተፈጠረበት ዓላማ ምን እንደሆነ እና ከዛ የተቃረነ እንቅስቃሴም ውጤቱ ምን እንደሆነ እግረ መንገድ የተብራራበት ነውና) እና የእግዚአብሔርን እውነተኛ ኖላዊነት ያብራራ ነው ። ክፋት የሰው ፈቃድ ከእግዚአብሔር ፈቃድ ሲፃረር የሚፈጠር ነው ። መቅሰፍቶችም ለንስሐ የሚያነቁ ወይም እምነት የሚፈተንባቸው መንገዶች ናቸው እንጂ በባሕርያቸው ክፉዎች አይደሉም ። ከዚህ በመጀመሪያ የምንረዳው ሰው ‘ሰው’ ሆኖ እንዲኖር እና የተፈጠረበትም ዓላማ ከግብ እንዲደርስ ፈቃዱን ከእግዚአብሔር ፈቃድ ጋር አስማምቶ መኖር እንዳለበት ሲሆን ሁለተኛው እግዚአብሔር ክፉ በሚመስሉ መግቦቶቹ ውስጥ ስንኳ መልካም እንደሆነ ነው ።

እንደማጠቃለያ ይህ ጽሑፍ ተቃርኖ ያለበት የሚመስል የመጽሐፍ ቅዱስ ጥቅስ የተብራራበት ብቻ ሳይሆን አንባቢውን ኦርቶዶክሳዊ ወደ ሆነው እይታ ፥ ይኸውም እግዚአብሔር ጨለማ የሌለበት ብርሃን ፥ ክፋት የሌለበት መልካም መሆኑንና በሱ መግቦት የሚፈቀድ ፈተና ሁሉ የኛን ፈቃድ ከእርሱ ፈቃድ ጋር ለማስማማት ስለ ጥቅማችን የሚፈቅደው መሆኑን ያብራራ ነው ማለት ይቻላል ። መጣጥፉን እንድታነቡት ለሌሎችም እንድታጋሩት በድጋሚ አሳስባለሁ ። መልካም ጊዜ!

Share...

Facebook
Telegram
WhatsApp
X
Email
Print
1 Comment
  • Abiy
    Abiy
    December 17, 2025 at 11:05 am

    እናመሰግናለን 🙏

    Reply
Leave a Reply to Abiy Cancel reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *

Related Posts

Guest Posts
መሐሪ ዘመልአክ

የአእላፋት ዝማሬ ምልክት ነው ።

መግቢያ በዘመናችን በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ የታየው “የአእላፋት ዝማሬ” የተባለው ክሥተት ሰፊ የሆነ ሕዝባዊና ሊቱርጊያዊ ውይይት አስነስቷል። አንዳንዶች ይህን እንቅስቃሴ እንደ መንፈሳዊ ንቃትና የራቁ ምእመናን ተሳትፎ መመለሻ ሲያቀርቡት፣ ሌሎች ደግሞ ከቤተ ክርስቲያን ትውፊታዊ ሊቱርጊያ[1] ጋር የሚጋጭ እና ሥርዓታዊ መነሻዋን የሚያዳክም ክዋኔ እንደሆነ ይገምግሙታል። ወንድማችን በርናባስ ሽፈራው የጻፈው “የአእላፋት ዝማሬ”ን የተመለከተ የኤማሁስ ገጽ ጽሑፍ አንዳንዶችን ሲያበሳጭ፣ ሌሎችን ሲያሳስብ እንደሰነበተ በአረቦን ቴሌግራም ቻነል ላይ ተመልክቻለኹ። 23 ገጾችን የያዘ፣ ንዑሳን አርእስት በግልጽ ያልተሰጡት ረዥም ጽሑፍ ስለኾነ ጊዜ ሰጥቶ ማንበብን፣ ካነበቡም በኋላ ዐበይት መከራከሪያዎቹን ማጥለልን ይጠይቃል። እንዲኽም ኾኖ፣ ቢያንስ መሠረታዊ የኾነ የሊቱርጊያዊ ነገረ መለኮት (liturgical theology) ንባብ ለሌለው ሰው ጽሑፉ ከንቱ ምቀኝነት፣ መራራነት፣ አማራሪነት፣ ጠብ ያለሽ በዳቦ ሊመስል ይችላል። በዋናነት እየነቀሰ የሚተቸው “የአእላፋት ዝማሬ”ን ልዩ ልዩ መልኮች ይኹን እንጂ፣ መሠረታዊ ጉዳዩ የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን በአኹኑ ጊዜ ያለችበትን ሊቱርጊያዊ ቀውስ (liturgical crisis) መጠቆም ኾኖ አግኝቼዋለኹ። ጉዳዩ እኔንም ሲያሳስበኝ የነበረ ነገር ስለነበረ የበርናባስን ሐሳብ እንዲኽ ልለጥቀው ወደድኹ። የእኔ ጽሑፍ የ“የአእላፋት ዝማሬ”ን እንደ ምልክት በመመልከት የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን በአሁኑ ጊዜ የምትገኝበትን ሊቱርጊያዊ ቀውስ ይጠቁማል። በተለይም በቋንቋ ባዕድነት፣ በዜማ ውስብስብነትና በሰዓት ምቹ አለመኾን ምክንያት ምእመናን ከ“ሰዓታት ጸሎት” የራቁበትን ኹኔታና ኮንሰርታዊ ዝግጅቶች በተግባር የተኩት የሊቱርጊያ ባዶ (liturgical vacuum) ምን እንደሆነ ለማመልከትና መፍትሔውን ለማሳየት ይጥራል። The Problem of Reactive Ministry እና Institutional Survivalism በርናባስ በጽሑፉ የሚተቸው አንዱ ነገር ይኽ ተልእኮን

Read More »
Emmaus Posts
በርናባስ ሽፈራው

“የአእላፋት ዝማሬ”

ሁለተኛው የአእላፋት ዝማሬ ባለፈው ዓመት በልደት ዋዜማ ተካሔደ ። በአዘጋጆቹ እና በተሳታፊዎቹ ዘንድ ይህ ሁለተኛው ዙር ከመጀመሪያው ዙር በላይ ያማረ እና የሠመረ ሆኖ ተቆጥሯል ። በጠቅላላው ከምእመናን በኩል በተሳትፎም ሆነ በማኅበራዊ ሚዲያ ያገኘው ተቀባይነት ሌሎች ሁነቶች ሲሆኑ እንደምናየው በጅምር የሚቀር ሳይሆን እንደ ባህል የመተከል ዕድሉ ሰፊ መሆኑን ያመላክታል ። እንዲያውም በአዲስ አበባ እና በድሬዳዋ ብቻ ሳይወሰን ወደ ሌሎች ቦታዎችም እንዲሰፋ የሕዝብ ጥያቄ እና በአዘጋጆቹም በኩል እቅድ መኖሩ ይታወቃል ። ስለዚህ በጥቂት ዓመታት ውስጥ ልክ እንደ ጥምቀት ሁሉ በሁሉም ዋና ዋና ከተሞች ውስጥ (የአዘጋጆቹ አቅም በፈቀደው ልክ) የአእላፋት ዝማሬ የልደት በዓል መለያ ሆኖ እንዲካሔድ መጠበቅ እንችላለን ። ይህ ነገር በብዙዎች ዘንድ ለቤተ ክርስቲያን ታላቅ ጥቅም የሚሰጥ ሆኖ ይታያል ። በእነርሱ ዐይን ይህ ሁነት ቤተ ክርስቲያን በብዙዎች ዘንድ እንድትታወቅ ያደርጋል ። ብዙዎች በዓሉን አስመልክተው ከሚሔዱባቸው የማይገቡ ዓውዶች ወደ ቤተ ክርስቲያን እንዲመለሱ ከማድረጉ ባሻገር ፥ በቤተ ክርስቲያን ሱታፌ ያላቸውንም በሚስብ እና በሚገባቸው መልኩ ቤተ ክርስቲያንን የበለጠ እንዲያውቋት ያስችላቸዋል ። ስለዚህም የሌሉትን በመጥራት ፥ ያሉትንም በማጽናት ቤተ ክርስቲያን ዘመኑን እንድትዋጅ የሚያስችላት መሣሪያ ነው ፤ ከእርሷ ዘንድ ወደ ክሕደት እና ወደ ኑፋቄ የፈለሰውን ፥ ወይም በስም ክርስቲያን ሆኖ እና ማዕተብ አስሮ ሳለ በምድራዊ ተድላ ባሕር የሰጠመውን ወጣት ወደ ራሷ የምትስብበት መረብ ነው ። ነገር ግን ከኖረው የቤተ ክርስቲያን ትውፊትና አስተምህሮ አንጻር ከመረመርነው ፥ ይህ ሁነት

Read More »
Emmaus Posts
መሐሪ ዘመልአክ

ከእውነት አልባነት ጋር የሚካሔድ ሙግት

(‘ሐሳቦች መዘዝ አላቸው’ በሚል ርእስ በኤማሁስ መጽሔት ቅጽ 1 ፣ ቁጥር 1 በወጣው ጽሑፍ ላይ የተጻፈ አስተያየት) በመሐሪ ዘመልአክ (PhD) ከዛሬ አሥራ አምስት ዓመታት በፊት የእጓለ ገብረ ዮሐንስ ‘የከፍተኛ ትምህርት ዘይቤ’ ለመጀመሪያ ጊዜ ካነበብኹ በኋላ ጸሐፊውን ከዚያ በፊት አለማወቄ ገርሞኝ እንደነበር አስታውሳለኹ ። ማን ናቸው ? እንዴት እስከዛሬ ድረስ ስለእርሳቸው ሳልሰማ ቀረኹ ? ለምን ? ይኼ በ1956 ዓ.ም. የታተመ የሬድዮ ንግግር ከኾነ መጽሐፍ ለመጻፍ ብለው ተነሥተው ቢጽፉ ኖሮ ምን ሊጽፉ ነበረ ? ወዘተ. የሚሉ ጥያቄዎች ጭንቅላቴ ውስጥ ተመላልሰዋል ።[1] በኋላ ፈላስፋው ኦርቶዶክሳዊ አማኝ ፣ የኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ተማሪና መምህር እንደነበሩ ስሰማ በመጽሐፉ ውስጥ ያየሁት የሐሳብ ጥልቀት በዘመኑ በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ልሒቃን ዘንድ የነበረው ተዋሥኦ ሊደርስ ይንጠራራበት የነበረውን ልክ የጠቆመኝ መሰለኝ ። ከዚያ በኋላ ያ የተዋሥኦ ልሕቀት የት ገባ ? እንዴት ድርቅና የተጫነው ተዋሥኦ ዋጠው ? እንዴት ኦርቶዶክሳዊነትን ከአመክንዮ የተፋታ እና አመክንዮን የሚፈራ ጭፍን እምነት የሚያስመስሉ የፎክሎር ሰባኪዎች ተፈለፈሉብን ?  የኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ካህን ለመኾን የሚጠየቀው መስፈርት ስለምን ድፍረት የለበሰ አላዋቂነት መሰለ ? በሚዲያ ላይ ሲናገሩ በአላዋቂነታቸው አንገታችንን የማያስደፉን ካህናት ስለምን ቁጥራቸው አልበረክት አለን ? ኦርቶዶክሳዊነት ችግርን እና ጭንቀትን ለማረሳሳት የተጠመቀ ዕፀ-ዝንጋዔ (‘opium of the masses’) እስኪመስል ድረስ በኦርቶዶክሳዊነት ስም የገነነው ተዋሥኦ ለምን አላዋቂነት ተጫነው ? ቤተ ክርስቲያን ሲባል ከስሜታዊ ሙጥኝታ (sentimental attachment) ባለፈ ለሰው ልጅ ህልውናዊ ጥያቄ የተሰጠ ከሞት ፍርኃት

Read More »
Emmaus Posts
ኤማሁስ

የኤማሁስ መንገድ

መጽሔቷን ለማግኘት ይህን ይጫኑ . . . የዘመናችን ተዋሥኦ በይዘቱም ሆነ በመንገዶቹ በግልብነት በእጅጉ የተጠቃ ነው ። ‘በይዘቱ እንዴት ?’ቢባል ሁነቶች ላይ ያተኮረ እና ወቅታዊነትን ማዕከል ያደረገ በመሆኑ ። አንድም አቋም ከመያዝና ጎራ ከፍሎ ከመናቆር ባለፈ የእውነት የመማር እና የማሰላሰል ጉጉት የማይታይበት በመሆኑ ። በዚህ ተዋሥኦ ውስጥ መሠረታዊ ጥያቄዎችን ማንሣት እና ከሁነቶቹ የሚሻገር እና ሐሳባዊ የሆነ ትንተና ለማካሔድ መሞከር ትኩረት ያስነሣል ፤ ሲብስም አጉል እንደመራቀቅ ይታያል ። የሚካሄድበት ከባቢ እና ዘመን ደግሞ ሌላ ግልብነት ደርቦለታል ። በእኛ ሀገር ብቻ ሳይሆን በሌሎችም ሀገራት ፣ ከዘመናዊነትና ከቴክኖሎጂ መራቀቅ ጋር ተያይዞ ሕዝባዊ ተዋሥኦ በጠቅላላው ስለቱን እና ርቀቱን እንዲያጣ ሆኗል ። የሚነበብም ሆነ የሚታይ ወይም የሚደመጥ ነገር አጭር መሆን አለበት ። ነገር ግን ጠቃሚና ወሳኝ ርእሶች እንዲህ ባለ መንገድ ሊስተናገዱ አይችሉም ። የሚያጠግብ ፍሬ ከሌለበት የተመልካቹ እና የአንባቢው ብዛት ምን ጥቅም ይኖረዋል ? እንዲህ ባለው ከባቢ ውስጥ ሁነቶችን ከሁነትነታቸው እና ከሚያመጡት ወቅታዊ ውጤት በተሻገረ መልኩ ለመመልከት እንቸገራለን ። ቀድሞውኑም (እይታችን ከመጥበቡ የተነሣ) ጠባብ አድርገን የቀረጽነውን አጀንዳ በምንገልጽበት መንገድ የበለጠ እናጠብበዋለን ። ነገር ግን ሁነቶችን እና ሒደቶችን ከመሠረታቸው መመርመራችን እና የምናቀርባቸው መፍትሔዎችም እንዲሁ የማይናወጥ መሠረት ያላቸው መሆናቸው አስፈላጊ ከሆነ ተዋሥኦውም እንዲሁ የጠለቀ እና የረቀቀ መሆን አለበት ። ይህን ለማድረግ ደግሞ ጊዜ ወስዶ ማሰብ ፣ ማንበብ ፣ ማጠናቀር ፣ መወያየት ፣ መሟገት እና እንዲህ ካለው ሒደት

Read More »
Emmaus Posts
በርናባስ ሽፈራው

ክፍል ፭ ፡ ወደ ርስታችን ያልተመለስንበት ኢዮቤልዩ

ሩሲያዊው ደራሲ ፌዮዶር ዶስቶየቭስኪ በ1860ዎቹ አውሮፓን ለመጀመሪያ ጊዜ ሲጎበኝ የታዘበውን በዘገበበት ማስታወሻው የለንደን ድሆች ቅዳሜ ማታን እንዴት ባለ መንገድ እንደሚያሳልፉ ይነግረናል ። በቅድሚያ ሌሊቱን በሙሉ ወንዶች ብቻ ሳይሆኑ ሚስቶቻቸውና ልጆቻቸው ጭምር ደስታ ፈጽሞ በተለየው ፣ ድብርት በተጫነው መንፈስ አኳዃን ሲበሉ እና ሲጠጡ ፣ ከሕይወታቸው መራራነት ለማምለጥ ፣ ራሳቸውን ፍጹም ለማደንዘዝ በሙሉ ጥምብዝ እስኪሉ እንደሚሰክሩ መስማቱን ይዘግባል ። ሳምንቱን ሙሉ ሠርተው የቋጠሯትን ገንዘብ ቅዳሜ ሌሊት እንዲህ ይበትኗታል ። አስከትሎም እንዲህ ባለው አንድ ምሽት እሱ ራሱ በመንደራቸው ውስጥ ሲያልፍ የታዘበውን እና የተሰማውን እንደሚከተለው ይመሰክራል ። “One such night – it was getting on for two o’clock in the morning – I lost my way and for a long time trudged the streets in the midst of a vast crowd of gloomy people, asking my way almost by gestures, because I do not know a word of English. I found my way, but the impression of what I had seen tormented me for three days afterwards. The populace is much the same anywhere, but there all was so vast, so vivid that you almost physically felt things which up till then you had only imagined. In London, you no longer see the populace. Instead, you see a loss of sensibility, systematic, resigned and

Read More »
Emmaus Posts
በርናባስ ሽፈራው

ብያኔን አሳልፎ ያለመስጠት ግዴታ

ከሁለት ሳምንታት በፊት ‘ከጥያቄዎቹ በላይ አደገኛ የሆኑት መልሶች’ በሚል ርእስ አንድ ጽሑፍ አቅርበን ነበር ። ጽሑፉ በዋናነት ማሳነስ (reductionism) የተባለውን ፅንሰ ሐሳብ የሚያነሣ እና የሚተች ነው ። በዚህ ጽሑፋችን ውስጥ መምህር ያረጋል አበጋዝ በቅርቡ ‘ወደ ላይ አያዳልጣችሁ’ በሚል ርእስ ገዳማዊ ሕይወትን ከዘነበ ወላ ዘለፋ ለመከላከል ጽፎ ያጋራውን ጽሑፍ ተችተናል ። ርእሱን በዚህ ጊዜ ጉዳይ ያደረግነውም በዋናነት በምምህር ያረጋል ጽሑፍ ምክንያት ነው ። በተለይ ጽሑፉ ሰፊ ተነባቢነት እና ተቀባይነት ያገኘ እንደ መሆኑ በውስጡ ያየነውን የማሳነስ ዝንባሌ መተቸቱ ጠቃሚ ይሆናል ብለን አመንን ። ነገር ግን የመምህር ያረጋል ጽሑፍ መነሻ ቢሆነንም በይበልጥ ፅንሰ ሐሳቡ ላይ ለማተኮር ነው የሞከርነው – ዓላማችን ነገሩ ላይ ተዋሥኦ እንዲጀመርና የተሻለ መረዳት እንዲፈጠር ማድረግ ስለሆነ ። መምህር ያረጋልም ጽሑፉን ተመልክቶ ምላሽ ሰጥቶናል ። ምላሽ በመስጠቱ ደስ ብሎናል ። በምላሹ ግን አልተደሰትንም ። አለመደሰታችን እኛ በእርሱ ጽሑፍ ላይ ያቀረብነውን ትችት ባለመቀበሉ አይደለም ። ይልቁንም የተሰጠው ምላሽ ከእኛ ትችት ጋር እምብዛም የተያያዘ ባለመሆኑ እንጂ ። ከነገሩ ጋር የማይገጥሙ ምሳሌዎች ቀርበዋል ። ያቀረብነው ሂስ በተሳሳተ መንገድ ተተርጉሟል ። በጽሑፋችን በስም ጠርተን ያራቅነው እና ያነወርነው ሐሳብ የእኛ አቋም ተደርጎ ተገልጧል ። “ለቤተ ክርስቲያን ከልባችን ከመጨነቅና ከመቅናት” ተነሥተን “ያልተባለውን ለማስመሰል በመድከማችን” ተወቅሰናል ፤ ዕጣችን ሆኖ “ሳንነቅፍ መጻፍ አልቻልንምና” ። እነዚህ ሁሉ ነገሮች መልስ እና እርማት የሚሹ ሆነው አግኝተናቸዋል ። አንድም ለእኛም ሆነ ለመምህር ያረጋል

Read More »