አባ ሶፍሮኒ የተባሉት የምስራቅ ኦርቶዶክስ መነኩሴ በፈረንጅ አቆጣጠር በ1947 ዓመተ ምሕረት ግሪክ ከሚገኘው አቶስ ገዳም ተነስተው ጥቂት መነኮሳትን ይዘው ገዳም ለመመሥረት ወደ እንግሊዝ ሃገር ሊገቡ ሲሉ ቪዛ ተከለከሉ ። የተከለከሉበት ምክንያት ገዳምም ሆነ መነኮሳት ለእንግሊዝ ሊሰጡ የሚችሉት አንዳች ነገር የላቸውም የሚል ነበር ። ለዚህ ክልከላ የአባ ሶፍሮኒ ምላሽ የሚከተለው ነበር “ኢየሱስ ክርስቶስ ከአሥራ ሁለቱ ሐዋርያት ጋር ወደ እንግሊዝ መጥቶ ቪዛ ቢጠይቅ ኖሮ መንግሥት ምን ያደርግ ነበር ?”[1] ከዚህ ምላሽ በኋላ ቪዛ ተሰጥቶአቸው በእንግሊዝ ሃገር ገዳም መሠረቱ ።
የአባ ሶፍሮኒ መልስ ሁሌም ያስደንቀኛል። የሚያስደንቀኝ ቁጥብነቱ ነው ። አባ ሶፍሮኒ “ግድ የለም ቪዛውን ብቻ ስጡን እንጂ ለሃገሪቱ ኢኮኖሚ የበኩላችንን አስተዋጽዖ እናደርጋለን ፣ እንደምታስቡን ሥራ ፈቶችና ሰነፎች አይደለንም ፣ የልማት ሥራዎች እንሰራለን” ወዘተ ሊሉ ይችሉ ነበር ። እንዲያ ቢሉ ውሸትም አይሆንባቸውም ፤ ቪዛውን የማግኘት ዕድላቸውም ይሰፋል ። ስለዚህ ለአገልግሎታቸው መቃናት ሲሉ እንዲያ ሊመልሱ ይችሉ ነበር ። ነገር ግን አላደረጉትም ። ምክንያቱም የመጡበት ምክንያት ያ አልነበረምና ። ክርስትናም ሆነ ገዳማትና ምንኩስና አንዳች “የሚታይ ቁሳዊ ጥቅም” ለማስገኘት አልተመሠረቱም ። ብቸኛው የመኖራቸው ምክንያት ጌታችን እና ሐዋርያት የፈጸሙትን ተልእኮ ማስቀጠል ነው ። ስለዚህ ምንም እንኳን በአንድ ወይም በሌላ አጋጣሚ አባ ሶፍሮኒን ቪዛ የከለከሏቸው ሰዎች “ዋጋ አላቸው” ብለው ያሰቧቸውን ዓይነት ተግባራት ቢያከናውኑም – በእነዚህ ተግባራት መመዘንን ግን ሊፈቅዱ አይችሉም ። እነዚህ ተግባራት – ለዋናው ተልእኮ መሳካት አስፈላጊ ካልሆኑ በስተቀር – በራሳቸው ለክርስትናም ሆነ ለገዳማዊ ሕይወት ምንም የሚጨምሩት ነገር የለምና ።
በዘመናችን ደጋግመን ፣ ሳናስተውል ከምንሰራቸው ስሕተቶች አንዱ ይህ ይመስለኛል ። ቤተ ክርስቲያንን ተልእኮዬ ነው ባላለችው ፣ ነገር ግን “ዘመናዊው” ዓለም አስፈላጊ ናቸው ባላቸው ነገሮች መሠረት ለክተን የቤተ ክርስቲያን “አበርክቶ” ፣ በማኅበረሰቡ ውስጥ ያላትን “ወሳኝ ሚና” ለማሳየት እንሞክራለን ። ኢኮኖሚያዊ ዕድገትን በማምጣት ፣ አካባቢን በመጠበቅ ፣ ማኅበራዊ መስተጋብርን በማበርታት ፣ ለባሕል መዳበር አስተዋጽዖ በማድረግ ፣ ኢትዮጵያን ለዓለም በማስተዋወቅና ቱሪስቶችን በመሳብ ወዘተርፈ ቤተ ክርስቲያን “የምታበረክተውን አስተዋጽዖ” እንቆጥራለን ። እነዚህ ሁሉ ነገሮች ግን ከቤተ ክርስቲያን ተልእኮ ጋር ምንም ግንኙነት የላቸውም ። ወይም ቤተ ክርስቲያን እነዚህ ነገሮች ለማሳካት አስባ የሠራችው ነገር የለም ። እነዚህ ሁሉ ቢሆኑም ባይሆኑም ለቤተ ክርስቲያን ምንም ልዩነት የለውም ። ይልቁንም ከቤተ ክርስቲያን ውጭ ያለው ዓለም ዋጋ ስለሰጣቸው ፣ እኛም ይህን ዋጋቸውን ስለተቀበልናቸው ነው ቤተ ክርስቲያንን በዚህ ሚዛን ለመመዘን የምንነሣው ። ይህ ዓይነቱ ቤተ ክርስቲያንን የእርሷ ተልእኮ ባልሆነ እና ምድራዊ በሆነ ሚዛን የመለካት አዝማሚያ reductionism ተብሎ ተጠርቷል ። እውነትም አዝማሚያው ከዓለም የሰፋችውን ቤተ ክርስቲያን ወደ ዓለም የሚያጠብ ፣ የሚያሳንስ እና በዓለም አጭር ጣሪያ ልክ እንድታጎነብስ የሚያስገድድ ነው ። አሌግዛንደር ሽሜማን የተባሉትን የምሥራቅ ኦርቶዶክስ ሊቅ ለመጥቀስ “ቤተ ክርስቲያንን በዓለም መነጽር ፣ በዓለም ፍልስፍናዎች ፣ በፋሽኖቹ እና በፍላጎቶቹ አንጻር በመመልከት እና በመመዘን በመጨረሻም ጨርሶ ለዓለም ማስገዛት ማለት ነው ።”[2]
ይህ አዝማሚያ ከእኛ ጋር በእጅጉ ከመዋሃዱ የተነሣ ብዙ ጊዜ እንደ ችግር ራሱ አንመለከተውም ። ይልቁንም አንድ አስፈላጊ ፣ ሊጠና እና ዝግጅት ሊደረግበት የሚገባው የዕቅበተ እምነት ዘርፍ ተደርጎ ተወስዶኣል ። “በስኬት” ሲሠራም በእጅጉ የሚደነቅ ሆኗል ። ዐበይት ከሚባሉ የዕቅበተ እምነት ድምጾች ሳይቀር ይህ ዓይነቱ ክርክር ተደጋግሞ ይሰማል ።
ለምሳሌ ከሰሞኑ ዘነበ ወላ የተባለው ደራሲና የአደባባይ ተናጋሪ ‘በእስልምና ምንኩስና የለም ፣ ይልቁንም በሥራ የሻከሩ እጆችን ያበረታታል’ ማለቱን ተከትሎ ሁካታ ተፈጥሮ ሰነበተ ። ዘነበ እስልምና ውስጥ ምንኩስና የለም ካለ በኋላ ስለ እስልምና የሥራ ባህል ጠንካራነት የተናገረው የምንኩስና ትውፊት ከሥራ የተፋታና ከስንፍና ጋር የተቆራኘ ነው ብሎ በማመኑ እንደሆነ ግልጽ ይመስለኛል ። ብስጭቱን በልዩ ልዩ መንገድ ሲገልጽ የነበረው አብዛኛው ሰው የዘነበን ሃሳብ አልሳተውም ።
ነገር ግን ይህን የዘነበን ነቀፋ ለመመለስ የተሔደበት መንገድ ቤተ ክርስቲያንን ዘነበ ወደ ተጠቀመው መለኪያ የሚያሳንስ ሆኖ አግኝቼዋለሁ ። ብዙዎች ያነበቡትን የወንድማችንን የመምህር ያረጋል አበጋዝ ምላሽ እንደ ምሳሌ ማንሳት ይቻላል። መምህር ያረጋል ምላሹን የጀመረው እንደሚከተለው ነበር ።
“ምናኔያዊ ሕይወት ፣ ከትንሣኤ በኋላ የምናገኘውን እንደ መላእክት የምሆንን ሕይወት ፣ በዚህ ዓለም ገንዘብ የማድረግ ሕይወት ነው ። ‘በትንሣኤስ እንደ እግዚአብሔር መላእክት ይሆናሉ እንጂ አያገቡም ፣ አይጋቡምም’ እንዳለ ጌታችን ። ማቴ. 22:30 መላእክት በተፈጥሯቸው እንደማያገቡና እንደማይጋቡ ሁሉ ፣ ከትንሣኤ በኋላ ደግሞ ለሰዎችም ማግባትና መጋባት እንደማይኖር ሁሉ ፣ መላእክት ዛሬ የሚኖሩትን ፣ የሰው ልጆች ደግሞ ከሞት በኋላ የሚያገኙትን ሕይወት መናንያን ገዳማውያን በአሁኑ ሕይወት ይኖሩታል ። እንደዚሁም ምናኔያዊ ሕይወት አዳም ከመበደሉ በፊት የነበረው ሕይወት ምን ይመስል እንደነበረ በመስታወት የሚያሳይ ነው ፣ ጌታችን የሰጠውንም ሕይወት በምልዓት የሚያሳይ ነው ።”
ይህ ምላሽ እውነት እና ትክክል ነው ። ዘነበ ወላን የሚያሳምነው ወይም ራሱን ትንሽም ቢሆን እንዲጠራጠር የሚያደርገው ባይመስለኝም ቅሉ ። ዘነበ ወላ – ዝም ብላችሁ ገምት ብትሉኝ – በመላእክት መኖር አያምንም ፥ ስለዚህ መምህር ያረጋል የገለጠው የመላእክት አኗኗር ለሱ ትርጉም የለውም ። መላእክት እንዳሉ እንኳን ቢያስብ “እጆቻቸው ሻካራ ስላይደሉ” አኗኗራቸውን ሳያቃልለው አይቀርም ። ዋናው ነጥብ የክርስትናን መሠረታውያን ለማይቀበል ሰው ምንኩስና “ሥራ ፈትነት” መምሰሉ አይቀሬ መሆኑ ነው ። ነገር ግን ይህ ምላሽ ለዘነበ ወላ ባይጠቅመውም የምንኩስናን ምንነት አማኝ ለሆኑ ሰዎች በአጭሩ ሊያብራራ ይችላል ። ነገር ግን መምህር ያረጋል ምላሹን በዚህ አላበቃም ። እንዲህ ሲል ቀጠለ ።
“ምናኔያዊ ሕይወት በክርስትና ውስጥ ያለውን እጅግ የገዘፈና ዘርፈ-ብዙ የሆነ ነገረ-ሃይማኖታዊና መንፈሳዊ ፋይዳ ለጊዜው ብናቆየው እንኳ፣ ክርስቲያናዊ ገዳማት ለሰው ልጆች ያበረከቷቸው ኢኮኖሚያዊ፣ እውቀታዊና ታሪካዊ ጠቀሜታዎች እጅግ በጣም ብዙ ናቸው። ጥቂቶቹን እንኳ ብናስታውስ፤ ዩኒቨርሲቲዎችና አዳሪ ት/ቤቶች በዋናነት የተቀዱት ከገዳማት ነው ። የከፍተኛ ተቋማት ተማሪዎች ሲመረቁ የሚለብሱት ጋዋንና የሚደፉት ቆብ የገዳማትን ቀሚስና ሞጣህት እንዲሁም ቆብ የሚመስለው በአጋጣሚ አይደለም ።”
ይህ እና ከዚህ የቀጠለው ምላሽ ለምን ተገቢ እንዳይደለ ከመተንተኔ በፊት አንድ ጥያቄ ላምጣ ። ሕፃን ልጃችሁ የጓደኛው ወላጆች እንዳደረጉት ፣ መማሪያ ደብተር ፣ ቦርሳ ፣ ዩኒፎርም ወዘተርፈ ከምትገዙለት ይልቅ ታብሌት እንድትገዙለት ቢጠይቃችሁ ምን ትመልሱለታላችሁ ? በእርግጠኝነት መቼም ትምህርትም ቢሆን ታብሌት የሚሠጣቸውን አንዳንድ ጥቅሞች እንደሚሰጥ – እንደሚያዝናና ፣ ትምህርት ቤትም ቢሆን ጨዋታ እና መዝናኛ ወዘተርፈ እንዳለ በመግለጽ ጊዜያችሁን አታጠፉም ። ልጃችሁ ረዘም ላለ ጊዜ ትምህርት ቤት ሔዶ ለረዥም ሰዓት እንቅልፉን ፣ ድካሙን እየተቋቋመ ፣ የጨዋታ ፍላጎቱን እያፈነ ፣ የቤት ሥራ እና የክፍል ሥራ ስለ መሥራቱ እየተጨነቀ መዋሉ ለጊዜው የሚዋጥለት ላይሆን ይችላል ። ነገር ግን ወደፊት ይረዳዋል ብላችሁ ታስባላችሁ እንጂ ትምህርት ቤት ከታብሌት ባልተናነሰ የታብሌትን “ጥቅም” እንደሚሰጥ ነግሬ እደልለዋለሁ ብላችሁ ተስፋ አታደርጉም ።
እርግጥ ነው ዘነበ ወላ ላይ ልጃችን ላይ ያለን ሥልጣን የለንም ፥ ምንም እንዲያደርግ ወይም እንዲያውቅ ልናስገድደው አንችልም ። ነገር ግን ወደፊት አሁን የናቃቸውን እና ያጥላላቸውን ነገሮች እውነተኛ ትርጉም ይረዳል ብለን ተስፋ እናደርጋለን ፣ እንጸልይማለን ። ከወደደም ለማሳየት እንጥራለን ። ያም ሆነ ይህ ግን ልንደልለው አያሻም ። ይህን ለማድረግ ለቤተ ክርስቲያን እና ለተልእኮዋ ያለን ታማኝነት አያሰናብተንም ። ቤተ ክርስቲያንን ከተልእኮዋ ውጭ ባለ ነገር እንድትመዘን ልንፈቅድም ሆነ እኛ ራሳችን ልንመዝናት መፍቀድ አይገባንም ።
መምህር ያረጋል ያመጣው ክርክር ችግር ይህን የሚያደርግ መሆኑ ነው ። ቤተ ክርስቲያንን ዘነበ ወላ ባስቀመጠው ሚዛን መለካት ይጀምራል ። ቀጥሎ የሚላቸው ነገሮች እኮ እውነት ሳይሆኑ ቀርተው አይደለም ። ነገር ግን ቀድሞስ “ምናኔያዊ ሕይወት በክርስትና ውስጥ ያለውን እጅግ የገዘፈና ዘርፈ-ብዙ የሆነ ነገረ-ሃይማኖታዊና መንፈሳዊ ፋይዳ ለጊዜው” ለማቆየት ለምን ይስማማል ? የሚዘረዝራቸው “ኢኮኖሚያዊ ፣ እውቀታዊ እና ታሪካዊ ጠቀሜታዎች” ከቤተ ክርስቲያን ተልእኮ አንጻር “ጠቀሜታ” ሊባሉ ይችላሉ ? ዘነበ እነዚህን “ጠቀሜታዎች” ተረድቶ የገዳማትን አስፈላጊነት ቢቀበል ስምምነት ላይ ይደረሳል ማለት ነው ?
የገዳማቱም ሆነ የምንኩስና መኖር በዋናነት ዘነበ “ጥቅም የላቸውም” ብሎ ለሚያስባቸው ምክንያቶች ነው ። ሌሎቹ መምህር ያረጋል የዘረዘራቸው ነገሮች በጠቅላላ (ለዋናው ተልእኮ አስፈላጊ እስካልሆኑ ድረስ) ቢቀሩም ምንም አይጎዱም ። በጠቅላላው የዘነበን “ጥቅም የመስጠት” መረዳት አንጋራውም ፤ ስለዚህ የእሱን መረዳት ተቀብለን ልንጀምር አይገባንም ። እዚህ ጋ አጽንዖት መስጠት ያለብኝ ነገር ቤተ ክርስቲያን ስለ ፖለቲካ ፣ ኢኮኖሚ ፣ ማህበራዊ ጉዳዮች አይመለከታትም እያልሁ አለመሆኑን ነው። ማሳነስ (reductionism) ብለን እያነወርን ያለነው ባህልን ፣ ኢኮኖሚን ፣ ፖለቲካን በራሳቸው ግቦች አድርገን ቤተ ክርስቲያንን ለእነዚህ ግቦች የማስገዛትንና ለእነርሱ በምታደርገው “አስተዋጽዖ” መሠረት ለመዳኘት የመሞከርን ስሑት አካሄድ ነው ። እኛ ግን እነዚህን ሁሉ ነገሮች የምንመለከታቸው በቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ መነጽርነት መሆኑ እና ለቤተ ክርስቲያን ተልእኮ ተገዢ መደረግ የሚገባቸው እንደሆኑ ማመናችን መረሳት የለበትም ።
ታዲያ ይህን ሁሉ ስል ሊነሣ የሚችል ጥያቄ አለ ። ይኸውም ‘ታዲያ ዘነበ ወላ ዝም ሊባል ይገባዋል ? መልስ ሊሠጠው አይገባምን ?’ የሚል ነው ። መልስ ሊሰጠው ይገባል ። ነገር ግን በክርስትና ለማያምን ሰው የምንኩስናን ጥቅም ለማስረዳት መሞከር ከንቱ ነው ። የዘነበ ችግር ከዚህ ዓለም የዘለለ ዕይታ የሌለው መሆኑ ነው ። ጌታችን በጥቂት አሳ እና በጥቂት እንጀራ ብዙ ሺህ ሕዝብ ከመገበ በኋላ ሊያነግሡት እንደፈለጉት ፤ ጌታችንም “እውነት እውነት እላችኋለሁ ፣ የምትፈልጉኝ እንጀራን ስለ በላችሁና ስለ ጠገባችሁ እንጂ ምልክቶችን ስላያችሁ አይደለም ። ለሚጠፋ መብል አትሥሩ ፤ ነገር ግን ለዘላለም ሕይወት ለሚኖር መብል የሰው ልጅ ለሚሰጣችሁ ሥሩ ።”[3] እንዳላቸው ፤ ሰማያዊ እንጀራን መብላትን ግን እምቢ ብለው እንደተመለሱት ሰዎች ነው ።
የዘነበ ወላ ነቀፋ የተመሠረተው “ዋናው ቁሳዊ ብልፅግና ነው ።” ሚል ስሑት እሳቤ ላይ ነው ። ስለዚህ ከእሱ ጋ ልንሟገት የምንችለው ፣ ይህን ለቁሳዊ ብልፅና የሠጠውን ልዕልና ከየት እንዳመጣው በመጠየቅ ነው ። ይህ እና መሰል ጥያቄዎች መሠረታዊ ወደሆኑ ጉዳዮች ይወስዱናል ። እንደ ዘነበ ካሉ ሰዎች ጋር ልንነጋገር የምንችለውም በዚያ ደረጃ ብቻ ነው ። ለእንዲህ ዓይነቱ ተዋሥኦ ራሳችንን ለማዘጋጀት ግን ብዙ መድከም ይኖርብናል ። አማራጭ የለንም ። መሠረታዊ ነገሮች ላይ ያለንን ልዩነት ወደ ጎን ትተን ድንገት ከምንኩስና ትርጉም እና ከገዳማት ሚና ልንነሣ አንችልም ። ዘነበ ወላ ምንኩስናን እንዲረዳ እንጂ ባለበት ሆኖ የምንኩስና “አድናቂ” እንዲሆን የማድረግ ተልእኮ የለንም ።
አሁን በያዝነው የማሳነስ (reductionist) አካሔድ የምንቀጥል ከሆነ ግን ከላይ እንዳልሁት ቤተ ክርስቲያን ወደ ዓለም ሚዛን እንድታጎነብስ እናደርጋታለን ። ይህ ሁሉ በቅንነት እንደሚደረግ ግልጽ ነው ። ነገር ግን ቀስ በቀስ ሊሔድበት የሚችለው ርቀት በጣም አደገኛ ነው ። በመጀመሪያ እኛ ራሱ በዋናነት ከዓለም ይልቅ የቤተ ክርስቲያንን ሚዛን ሚዛናችን እንድናደርግ ስለሚያስገድደን “የዘመናዊውን” ዓለም ጥያቄዎች ቤተ ክርስቲያን ውስጥ እንድናመጣቸው ያስገድደናል (ልጃችሁ ትምህርት ቤት ሔዶ የሒሳብ ክፍለ ጊዜ ተቀንሶ በፊልም ክፍለ ጊዜ እንዲተካ ሲጠይቅ ይታያችሁ) ። ስለዚህም “ዘመናዊው” ዓለም ዋጋ ለማይሰጣቸው ፥ ግን የክርስትናችን መሠረት ለሆኑት ነገሮች ቀስ በቀስ ያነሰ ዋጋ እየሰጠናቸው እንድንሔድ እንሆናለን ። የሥነ ምግባር መረዳታችን ጭምር በቤተ ክርስቲያን ሳይሆን በዚህ ውጫዊ መረዳት እየተወረሰ ይሔድና – ቤተ ክርስቲያንን በዚህ ጉዳይ ለማረም ጭምር እንድንቃጣ ፣ ያደርገናል ።
አንድ አስረጅ ብንጨምር ያለንበት ዘመን የፌሚኒዝም ፍልስፍና እጅግ ያየለበትና ተዋሥኦዎቻችንን ሁሉ የቃኘበት ዘመን ነው። ሴኪዩላር ከሆነው ተዋስዖ አልፎ በቤተክርስቲያን ውስጥ ለሚጠየቁ ጥያቄዎች የሚመለሱትን መልሶች ስንመለከት የፌሚኒዝምን መሠረታዊ መርሖች ከመጠየቅና ውድቅ ከማድረግ ይልቅ እንዲያውም እነዚህን መርሖች የተቀበሉ ሆነው እናገኛቸዋለን ። ለምሳሌ ሴቶች በቤተክርስቲያን ውስጥ ያላቸው ድርሻ ምንድርነው? ከወንዶች ጋር እኩል ከሆኑ ለምን ካህናት አይሆኑም? የሚል የእኩልነት ብያኔውን ከቤተክርስቲያን ሳይሆን ከፌሚኒዝም ፍልስፍ” የቀዱ ጥያቄዎች ሲጠየቁ እንሰማለን ። ለእነዚህ ጥያቄዎች ደግሞ ፣ ባዕድ የሆነውን መረዳት ከማረም ይልቅ ፣ “እመቤታችንም እኮ ሴት ነበረች” ፣ “ቤተክርስቲያን ውስጥ እኮ ብዙ ቅዱሳን ሴቶች አሉ” ፣ “ቤተ ክርስቲያን የሴቶችን እኩልነት ታከብራለች” ወዘተርፈ የሚሉ አሳፋሪ መልሶች ሲሰጡ እንሰማለን ።
ይህ አካሄድ በእነዚህ አጋጣሚዎች የተገለጠ ብቻ ሳይሆን በጠቅላላው የዕቅበተ እምነት አካሔዳችን ላይ በሰፊው እየተስተዋለ ያለ ነው ። ከጥቂት ጊዜያት በፊት አንድ ፌስቡክ ላይ የሚጽፍ ብዙ አንባቢዎችም ያሉት ሰው ‘የድህነታችን ምንጭ የምኩስና ትውፊት ነው’ በሚል ለተሰነዘረ ትችት መልስ ሲሰጥ ፣ ሃይማኖተኞች ሃይማኖት አልባ ከሆኑ ሰዎች ይልቅ የተሻለ ሃብትና ደስታ እንዳላቸው የሚያሳይ አሜሪካ ውስጥ የተሰራን አንድ ጥናት በመጥቀስ ሃይማኖትን ሊከላከለው ሞከረ ። ጽሑፉ በጊዜው ብዙዎች ያነበቡትና የተቀባበሉት ነበር። ይህም ተመሳሳይ የቤተ ክርስቲያንን ተልእኮ የማሳነስ አካሄድ ነው ። ጸሐፊው በተቺዎቹ ወጥመድ ውስጥ መሰስ ብሎ እየገባና በእነርሱ ሜዳ እየተጫወተ እንደሆነ የተረዳ አልመሰለኝም ። ሃይማኖት አስፈላጊ እንዲሆን የተደላደለና ደስተኛ ህይወት መስጠት አለበት የሚለውን መቅድማዊ ሃሳብ (presupposition) ተቀብሎ ነው የጀመረው ። ያጣቀሰው ጥናት የተሠራበትን ነገረ መለኮታዊ መነሻም በቅጡ እንዳልተገነዘበ ግልጽ ነው ። ጥናቱ የክርስትና ዐላማ ሰዎችን ሃብታምና ደስተኛ ማድረግ እንደሆነ በመቅድማዊ መነሻነት የተቀበለ ነው ። ጸሐፊው ክርስቲያኖች ድሆችና ደስተኞች ያልሆኑባቸውን ሌሎች ጥናቶች ቢመለከት ምን ሊውጠው ነው? ወይስ በምናኔ እና በምንኩስና ያለውን የድህነትንና የፈተና ሕይወት እንዴት ሊረዳውና ሊያስረዳው ይሆን ? የሐዋርያትን የዘወትር ስደትና መከራ ፣ የሰማዕታትን “የዚህችን ዓለም ጣዕም መናቅስ” ? ወይስ የሐዋርያትና የሰማዕታት ጊዜ ማለፉን ማወጅ እና ገዳሞቻችንን “ሻካራ እጆች” እንዲሁም ደስተኛ እና የተደላደለ ሕይወት ባላቸው መነኮሳት መሙላት የሚገባን ጊዜ ደርሶ ይሆን ? የችግሩ መነሻ ያለው ክርስቲያኖች ክርስቲያን በመሆናቸው የተነሳ ደስተኛና ሃብታም ፣ በጥቅሉ ስኬታማ መሆን አለባቸው የሚለውን አስተሳሰብ ውድቅ አድርጎ መነሣት አለመቻሉ ላይ ነው። ቶማስ ሆፕኮ የተባለው የነገረ መለኮት ምሁር በአንድ ንግግሩ “ስኬት ኢኮኖሚያዊ እንጂ ነገረ ሃይማኖታዊ ቃል እና ፅንሠ ሐሳብ አይደለም”[4] የሚል ሃሳብ አሻግሮ ነበር ። ሙሉ በሙሉ እስማማለሁ ።
እንዲህ ያሉት መልሶች ከጥያቄዎቹ በብዙ እጥፍ የሚብስ አደገኝነት አላቸው ። ምክንያቱም ልክ የትሮይ ሰዎች የድላችን ሐውልት ነው ብለው ያሰቡት የእንጨት ፈረስ በውስጡ የግሪክ ወታደሮችን የደበቀ የጥፋት ወጥመድ እንደነበረ ሁሉ እንዲህ ያሉት የዕቅበተ እምነት መልሶችም እንዲሁ ድል ሊቀዳጁባቸው የፈለጓቸው ጥያቄዎች የተነሡባቸውን መሠረቶች ባለማስተዋል ተቀብለው ወደ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ የሚያስገቡ እና ቤተ ክርስቲያን ላይ ጥፋትን የሚጋብዙ በመሆናቸው ነው ።
በጣም አሳዛኙ ነገር የትሮይ ሰዎች ያን ፈረስ ወደ ከተማቸው ቅጥር ሲያስገቡ ድል ማድረጋቸውን አስበው እየፈነጠዙ እና በዓል እያደረጉ ነበረ ። ከአሥር ዓመታት ጦርነት በኋላ ድል አድርገን አረፍን ባሉባት ሌሊት ነበረ ሽንፈታቸው እና ጥፋታቸው በድንገት የደረሱባቸው ። ነገሮች በደፈረሱበት ዘመናችን ፣ እምነታችንን ለመጠበቅ እና ለቤተ ክርስቲያን ዘብ ለመቆም የምናደርገው ጥረት መልሶ የእምነታችንን እና የቤተ ክስቲያንን ህልውና እንዳይፈታተን መጠንቀቅ ይኖርብናል ። ሽሜማንን ዳግም ለመጥቀስ ፦
“በማንኛውም ጊዜ ቢሆን የነገረ ሃይማኖት ተግባር የሚወሰነው በቤተ ክርስቲያን መሻት ነው ። የመምህራን ቀዳሚ ሚናም እነዚህን መሻቶች ለይቶ ማወቅና መቀበል ፥ ቤተ ክርስቲያን የምትጠብቅበትንም ነገር መረዳት ነው ።”[5]
[1] “What would the government have done if Jesus had arrived in England with his twelve apostles, asking for a visa” – The mountain of silence (2011), chapter 3
[2]“evaluating the church in terms of the world, of its philosophies, of its trends and of its needs ultimately to a surrender to the world” – Alexander schmemann(1979), Church, World, Mission, p. 21
[3] ዮሐ 6፣ 26
[4] “Success isn’t a theological term, it’s an economical term”
[5] “The task of theology at any given moment is determined by the needs of the church and the first task of the theologian is always to discern and to accept those needs, to become aware of what the church expects of him.” – Alexander Schmemann (1979), p. 118






እግዚአብሔር ይስጥልን…አይምሮህን ይባርክልን።
ቃለ ሕይወት ያሰማልን ኤርሚ። በመጀመሪያ ዲያቆን ያረጋል አበጋዝ ከተለመደው በተለየ (Active ሆኖ) ጉዳዩን ጉዳዬ ብሎ መልስ መስጠቱ አስገርሞኛል።
ለእኔ የያረጋል ምላሽ publicly መዳረሱ ካልሆነ በቀር ሁኔታው ግዴታ በዚህ ልክ ወርዶ እንዲመልስ የጠየቀው ይመስለኛል። ዘነበ ወላ እይታውም ነገረ ሀይማኖት ላይ ያለው መረዳትም እስከየትኛውም ድረስ የተዛነፈ ቢሆንም ሊጸና ቀጥ ወዳለው መስመር ተስተካክሎ ሊገባ የሚገባው አንድ ጥሙቅ ምዕመን ነው። መምህር ያረጋል በይደር ይቆይ ብሎ ያለፈውን ጉዳይ ቢተነትነው ዘነበ ወላ ላይ የተለየ የሚፈጥረው ነገር አይኖርም። አውቃለው፣ ቤተክርስቲያን እና የሚያገለግሏት ያልተማሩ ማይማን ናቸው የሚል የተሳሳተ እሳቤ አለው። ምዕመን ስለሆነ መመለስ ስላለበት በቅድሚያ በተሳሳተ ሚዛኑ ያስቀመጠውን የተሳሳተ ልኬት አስተካክሎ አሳየው። ከሌሎቹ በበለጠ ለዘነበ ይህ የበለጠ እንዲረዳው የቀረበ እና ስህተቱን የሚቀበል ከሆነ በእርሱ አስተሳሰብ ደረጃ የሚመጥነው ቀዳሚው መልስ ነው።
ከስራም ባለፈ ለዘነበ እጅግ የተከበረ እና የተሻለ የሚያስብለው የዘመናዊ ትምህርት መካነ አእምሮ መገኛ እና መነሻ ምርቃታቸው ሳይቀር ከዛ መሆኑን ያስረዳውም ይህንኑ የታመመ የዘነበ ወላን ሀሳብ ለማከም ነው። ምናልባት በግል ቢገናኙ ኑሮ ከዚህ በኋላ የተወሰኑ ጥያቄዎቹን መልሶ የምንኩስናን ልዕልና ሰማያዊ ዓላማ ወደ ማስረዳት የሚሄድ ይመስለኛል። ለዚህ ቃልኪዳን በነገረ ድኅነት የመሰሉ መጻሕፍቱ ትንሽ የሚመስለንን ነገር እስከ መነሻ ምንጩ፣ ዋና ሥር ማዕከሉ ድረስ ገብቶ መመለስ የመምህር ያረጋል ጸጋው መሆኑን ያሳየናል።
” ዘነበ ወላ ምንኩስናን እንዲረዳ እንጂ ባለበት ሆኖ የምንኩስና “አድናቂ” እንዲሆን የማድረግ ተልእኮ የለንም። ” … ያልካት እጅግ መልካም እና የምጋራት ሀሳብ ናት። ዘነበ ወላ ግን በዋሊያ (ቤተመጻሕፍት) በተደረገ ጉባኤ ላይ ዲያቆን ዮሴፍ ለጠየቀው ጥያቄ ለመመለስ ያልቻለ እና ቤተክርስቲያን ላይ ጥያቄ እና ብያኔ ለመስጠት እንጂ ለመጠየቅ ያልተዘጋጀ ልቡ ያልተከፈተ ሰው መሆኑን አይተናል። እና ኤርሚ ዘነበን በመጠየቅ እርሱን ለማዳን የምንችል አይመስለኝም። እንደጠየቀው ጥያቄ አቃንተን እየመለስን ሚዛኑን እያስተካከልን እና ቢቻል ከወንድሞቹ አንዱ እያባባለ በትምህርተ ሀይማኖት ሊታከም የሚገባው ይመስለኛል።
ከታች ያነሳሃቸው ሀሳቦች ላይ በቤተክርስቲያናችን ላይ የሚታየው የReductionism ተጽእኖ በሚገባ በፖድካትም በብዙ ክፍል በጥልቀት ልትወያዩበት በዚህ በብሎግም ልትጽፉበት የሚገባ ትኩረት የተነፈገው ግን እየናደን ያለ እሳቤ ነው። መምህር ያረጋል ከዋናው ይልቅ በጠያቂው ሚዛን ልክ ሄዶ የማስተካከል ሥራ ላይ የሄደው ግን ዘነበ ወላ ካለበት ሁኔታ አንጻር ከሌሎቹ የተመቸ አካሄድ ስለሆነ ነው ብዬ አስባለው።
እይታህን ጥሩ ነው
እኔ የመምህር ያረጋል ጽሑፍ ያን ያህል ትችት የሚያስፈልገው ጽሑፍ ሆኖ አላገኘሁትን፣
Wendime ermiyas endihum leloch ye emmaus press azegajoch enaten lasinesa amilak kiber misgana yigbaw
Hulachininim mechereshachin siyamir new kiluna mechereshachihun yasamirew EGZIYABHER AMLAK yitebikachu!!!
Bertu misganaya lak yale new emigerim eyita ena ewineta new
Beirachu Ayintef!
በሀሳቡ ከሞላ ጎደል እስማማለሁ፣ አርቆ ማጠር መልካም ስለሆን፣ ከዕቅበተ እምነት አንጻር ካየነው፡ ግን የያረጋልን ጽሁፍ ጉድለት አላየሁበትም!!
የመምህር ያረጋል ምላሽ መልካም ነገሮች እንዳሉት ባይካድም በሌላ አቅጣጫ ሊስተዋሉ የሚገባቸውን
ድክመቶች አጉልተህ ስላሳየኸን እግዚአብሔር ይስጥልን!
በርታልን
ዋው በዚህ ርቀት አስቤው የማላውቀውን ሃሳብ ነው ያጋራቹን።ተባረኩ ቀጥሉበት ወገኖቼ 🙏🙏🙏🙏
ልክ ጌታችን እንዳደረገዉ ሰዉን እንደአጠያየቁ ለመመለስ ነዉ ምህራችን ለማስረዳት የሞከሩት
በዚህ ዘመን ለሹመትም ለሽልማትም የደብር አለቆችን የሚያፈጥናቸው ህንፃ ግንባታ እና በየትኛው መንገድ ብር መሰብሰብ ነው ። መንፈሳዊው ተግባር እጅጉን ተንቋል ተረስቷል።
ግሩም እይታ ነው:: በጣም ብዙ ነገር ተማርኩበት ቃለሕይወት ያሰማህ::
በመጀመሪያ እግዚአብሔር ይስጥልኝ፡፡
ምን ግዜም ቢሆን መንፈሳዊ እሳቤዎችን ወደ ዓለማዊ እሳቤዎች ማውረድ የራሳችንን የዕምነት ልኬት ምን ያክል ጎዶሎ አንድ አንድ ግዜም እምነት የለሽ መንፈሳዊ እሳቤዎች ውስጥ ጭልጥ ብለን የገባንና ፐ ለመባል ብቻ የተሰበሰብን የእምነት አሰመሳይነት የተጸናወተን መንፈሳዊ እሴታችንን ባልተሻለ መንገድ የምንመነዝር ይመስለኛል፡፡ ፅሑፉ በጣም ተጠቀለለ እንጂ reductionism ከመንፈሳዊነት አንጻር በብዙ ቦታዎች ላይ የሚስተዋል ነውና በደንብ ሊተነተንና እንደውም ጠለቅ ያለ ምርመራ የሚያሰፈልገውና ለጎዶሎ አሳቢነታችን ምሉዕ የሆነ ነገር በድጋሜ ቢቀርብ ደስ ይለኛል፡፡ በተቀረ እግዚአብሔር ያበርታችሁ፡፡
Kalehiwot Yasemalin!
Paragarafochu yetewakerubet, yetsihufu firehasab tiru new end tsihuf malete new neger gin keteneseaw tiyake antsar(ke Zenebe Wella) tichit ena ke D/N Yaregal melsoch antsar analyse saregew yante hasaboch ende and anbabi yanyahil wuha yemianesa huno algegnehutim.
Mikniatum
#. Zenebe Wella yanesaw tichit Islimina wust Minkusina, yeminane hiwot Yelem, titeraleh timetaleh tisegdaleh timelesaleh keza wede sira tisemaraleh new yalew silezih lezi melsoch sile Betekiristian lemenfesawi hiwot asfelaginet masredat new yemishalew weyis Betekiristian lesigawihiwot litaberekit yemitchilewn ena yabereketechiwun masredat new yemishalew?
#. Kezi ansar Zenebe Wela yegbawm ayigabawm Betekiristian lemenfesawihiwot yemitaberekitewn hiwot D/n Yaregal bedemb asreditual biyenew yemamnew. Kelay yetekeskachew negeroch hulum yesiga fire nachew economiawi mahiberawi wezete yalkachew hulu Betekiristian yetemeseretechiw yehizbun economiawi chigir fetita be economy hageritun lemafertem sahun ye Egzabhern serawit be amliko lemafertem new. Egremengeduan gin ye hizbun economiawi ena mahiberawi chigirun bitfeta kifat yelewm. Wanaw sirawa gin economy adelem menfesawinet new. Zenebe Wella Gedamtinena Gedamawiyanin endesirafet silekotere esun minanagiribet kuankua laygebaw yichilal tebilo bealemawi kuankua manager yalebin aymeslegnim. Egna masredat yalebin wanawun targetachin focus argen enji egremengedachin weyim behuletegnaw sirachin esu yasilemigebaw bicha beza manager yelikunm Betekiristianin be Alem melekat yemihonew ena adegegnaw akahed ante yezerezerkachew nachew. Sile Betekristian tikim kemasredat yelik egremengedun lehizbu econemiawi mahiberawi akababiawi(environmental) lay tiseralech, kebt tarebalech, zaftiteklalech eyaln binzerezir kiristinan kemasfafat ena kiristianochin kemafrat antsar enezih negeroch astewatsoachew mindinew?
ተባረክ እንዲ ያሉ ጥልቅ የየሆኑ ትችቶች ያስፈልጉናል
እነ ኤርሚያስ ወንድሞቻችን እንደምን አላችሁ ?! ወጣትነት ከሚያስከትላቸው የሕይወት ፈተናዎች ውስጥ አንዱ ኹሉን ልብላው የሚል እሳታዊ አካሔድ አንዱ ነው። ይኽ የተፈጥሮ ግዴታ ዕውቀትና ዕቅበተ እምነት በሚመስል መልኩ የማይበላውን ኹሉ ልብላ ወደሚል ድፍረት ሊመራ ይችላል። ኹሉም ነገር በኹሉም ቦታና ኹኔታ አይተችም።
በመምህር ያረጋል ጽሑፍ ላይ የሰጣችሁን አስተያየት ኹለት ችግሮች ታይተውኛል። አንደኛ መምህር ያረጋል በመልሱ ላይ ስሕተት ፈጽሟል ብላችሁ የሰነዘራችኋቸው ዐሳቦች በሙሉ በዳበረ መንገድ በመጽሐፉ መ.ጽ ቅጽ ፫ በሥነሥርዓቱ ገልጿቸዋል። ለትች ጽሑፍ ከመሮጥ የመምህር ያረጋልን ውሳጣዊ አስተሳሰብ ለዘነበ ወላ የሰጠውን ምላሽ በመ.ጽ ከጻፈው ዐሳብ ጋር አናቦ መረዳት እና እኛ ያልደረስንበት ዐተያይ ኖሮት ቢኾንስ ከሚል ትሑት ዐሳብ ጋር ማገናዘብ ይሻል ነበር።
ኹለተኛ ዐቃቤ እምነት እንደመኾናችሁ ዕቅበተ እምነት ሥርዓት እና ደርዝ ያለው ነው። በችኮላ የሚሰጥ የዕውቀት ማሳያ ወይም ብስጭትን መግለጫ አይደለም። አንድም እንጂ ዕቅበተ እምነት ትሕትና፣ ታላቅን ማክበር ነው። እንጂ በዕቅበተ እምነት ስም የብርዕ መዓት ሰይፍ በኹሉም ላይ መምዘዝ አይመስለኝም።
https://emmauspresset.com/829/
በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!
ጥቂት ሃሳብ ለመስጠት!
ዕይታችሁ መልካም ነው ነገርግን እንዲሁ አየር ላይ ከመነቃቀፍ ይልቅ መምህራችን ለሁሉም ነገር ቅርብ እንደሆኑ አውቃለሁ (ለትችትም፣ለውይይትም፣ለጥያቄና መልስም… )ስለዚህ ሳትገፋፉ ብትነጋገሩ መልካም ይመስለኛል!
ለቤተክርስቲያን ሥርዓት መቆም የሚያስመሰግንና የሚጠበቅ ሐዋርያዊ ግዴታ ሆኖ ሳለ ፈሊጥ ቢኖረው ደግሞ መልካም ነው!!!
ብትችሉ የአየር ሰዓት ሰጥታችሁ ከመምህራችን በጋራ ብትሠሩና ብትተጋገዙ መልካም ፍሬን ማፍራት ይቻላል ብዬ አስባለሁ!
በተረፈ የእናንተን ሃሳብ በእጅጉ የምጋራውና ልንሠራበት የሚገባ መሆኑ ምንም ጥያቄ የለውም!
በእኔ መራዳትም መምህራችን ዲ/ን ያረጋል የሰጡት መልስ ለዘነበ እንደአቅሙ ‘ወተት’ ብለው ይመስለኛል እንጂ ነገርን ከሥር መሠረቱ በማስተማርና በመጻፍ የምናውቃቸው ናቸው።
የእናንተ ዕይታ ለጠነከሩት የመምህራችን የመለሱት ደግሞ ለዘነበ በሚመጥነው ልክ የተሰጠ ይመስለኛል ሁለቱንም ብንጠቀም ግን ከታች ተነስተን ወደፍጹም ዕውቀት መድረስ ይቻለናል በአንድ ጊዜ ወደፍጹም ዕውቀት መድረስ አይቻለንምና በምናያቸውና በምንሰማቸው ላይ ተነስተን ወደላይ ብንወጣ ፍሬ እናፈራለን በርቱ!
ስለዚህ ሁላችሁም ለሥርዓተ ቤተክርስቲያን ብላችሁ እየደከማችሁ እንደሆነ ግልጥ ነው እናም እኛ እምብዛም ብስለት የሌለን በእናንተ መገፋፋት እንዳንጎዳ አንድ እንሁን!
እግዚአብሔር ይስጥልኝ